በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በሺሕዎች የሚቆጠሩ ከሱዳን ተመላሽ ኢትዮጵያውያን በመተማ


በሺሕዎች የሚቆጠሩ ከሱዳን ተመላሽ ኢትዮጵያውያን በመተማ
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:48 0:00

በሺሕዎች የሚቆጠሩ ከሱዳን ተመላሽ ኢትዮጵያውያን በመተማ

ባለፈው ዓመት በሱዳን የተፈጠረውን ግጭት ሸሽተው በመተማ በኩል የተመለሱ ኢትዮጵያውያን፣ ወደቀዬአቸው እና የትውልድ ስፍራዎቻቸው ገና አለማምራታቸውንና በዚያው በመተማ እና በሌሎች የአቅራቢያ ከተሞች ለወራት እንደተቀመጡ መኾኑን ገልጸዋል፡፡

ተመላሾቹ፣ እስከ አሁን በቂ ርዳታ አለማግኘታቸውን ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።

በመተማ፣ በደባርቅ እና በጃን አሞራ ወረዳዎች፣ በመጠለያ ጣቢያ እና ከማኅበረሰቡ ጋራ ተቀላቅለው የሚገኙት ተመላሾቹ፣ “በመንግሥት አልተጎበኘንም፤ ከዓለም አቀፍ ረጂ ድርጅቶችም በቂ ድጋፍ አላገኘንም፤” ብለዋል፡፡

አያይዘውም፣ ወደ ትውልድ ቀዬአቸው ለመመለስ፣ በክልሉ ያለው ጸጥታ፣ ድርቅ እና ሌሎች ችግሮች ዕንቅፋት እንደኾኑባቸው ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል፡፡

የአማራ ክልል አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ኮሚሽነር ዲያቆን ተስፋው ባታብል በበኩላቸው፣ ፍልሰተኞችን ለመደገፍ ግምገማ እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ለ13 ዓመታት በሱዳን - ካርቱም በግል ሥራ ይተዳደር እንደነበር በስልክ የገለጸልን ዮሐንስ አስረስ፣ ባለፈው ዓመት በሱዳን በተቀሰቀሰው የእርስ በርስ ጦርነት ምክንያት፣ ሁለት ልጆቹን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሰ በኋላ አሁን በመተማ መጠለያ ጣቢያ እንደሚገኝ ነግሮናል፡፡

ዮሐንስ፣ ዛሬ ረቡዕ ለአሜሪካ ድምፅ እንደገለጸው፣ እስከ አሁን በቆየበት የመተማ መጠለያ ጣቢያ፣ ከዓለም አቀፍ ረጂ ድርጅቶችም ይኹን ከመንግሥት በቂ ድጋፍ አላገኘም፡፡

በዚኹ መጠለያ ጣቢያ የሚገኘው ሌላው አስተያየት ሰጭ አብርሃም ዓለሙም፣ በጣቢያው ውስጥ በቂ የምግብ አቅርቦት እንደሌለ ተናግሯል።

በአንጻሩ፣ የአማራ ክልል አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ኮሚሽነር ዲያቆን ተስፋው ባታብል፣ እስከ አሁን በመተማ የተቀመጡት ፍልሰተኞች፣ ወደየአካባቢያቸው መመለስ ያልፈለጉ ናቸው፤ ብለዋል።

በደባርቅ ከተማ ከማኅበረሰቡ ጋራ ተቀላቅለው እንደሚኖሩ የገለጹልን ከሱዳን ተመላሹ ፍቅሩ ታደሰ፣ እርሳቸውን ጨምሮ አራት ሺሕ የሚደርሱ ፍልሰተኞች በከተማው ውስጥ

እንደሚገኙና አስከፊ ኑሮ በመምራት ላይ እንዳሉ አስረድተዋል፡፡ ከቤተሰቦቹ ጋራ ለመኖርም የቤተሰቡ ብዛት አዳጋች እንደኾነበት አመልክቷል፡፡

በጃን አሞራ ወረዳ ከቤተሰቦቹ ጋራ እንደሚኖር የነገረን ሌላው ተመላሽ ግርማው ጌታቸው፣ ለአንድ ዓመት ሙሉ ምንም ዐይነት ድጋፍ አግኝቶ እንደማያውቅ ተናግሯል፡፡

የክልሉ አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ኮሚሽነር፣ በደባርቅ እና በሌሎች አካባቢዎች የተጠለሉ ፍልሰተኞችን ለመደገፍ ግምገማ እየተደረገ ነው፤ ብለዋል፡፡

በሱዳን የቀጠለውን ግጭት ሽሽተው በመተማ በኩል ወደ አገራቸው ከተመለሱ ኢትዮጵያውያን 3ሺሕ848 የሚኾኑቱ፣ እስከ ዘጠኝ ወር ገደማ በዚያው በመተማ ለመቆየት መገደዳቸውን፣ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በምኅጻሩ ዩኤን-ኦቻ፣ ባለፈው ሳምንት ዐርብ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

በደባርቅ ከተማ ከአራት ሺሕ በላይ፣ እንዲሁም በጎንደር፣ በባሕር ዳር እና በሌሎች አካባቢዎች ደግሞ፣ ቁጥራቸውን በውል ያልገለጻቸው ፍልሰተኞች እንደሚገኙ፣ ከክልሉ አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG