በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች ተማሪዎች የመብት ጥያቄዎችን አንስተው ተቃውሞ አሰሙ


የተማሪዎቹ ጥያቄዎች የተለያዩ መልክ ያላቸው ናቸው። ዛሬ ማምሻውን አዲስ አበባ ከተማ የትምህርት ነጻነታችንን የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ተጋፍቶናል ሲሉ በመቶዎች የተቆጠሩ የአወሊያ የመለስተኛ፣ ሁለተኛ ደረጃና ኮሌጅ ተማሪዎች ድምጻቸውን በማሰማት ላይ ናቸው።

ጥያቄዎቻችን ካልተመለሱ ወደቤታችን አንሄድም በሚል በትምህርት ቤቱ ቅጥር ግቢ ዛሬ ሊያድሩ የወሰኑት ተማሪዎች፤ ቁጥራቸው ከ600 በላይ እንደሆነ ይናገራሉ። ለአንድ ሳምንትም ትምህርት ተቋርጧል።

“ምንም አይነት ችግር ሳይፈጠር ኮሌጁን የእልምና ጉዳዮች ዘግቶብናል፣ የኮሌጁ መምህራንና ዲኖች ከስራ ተሰናብተዋል፣ እንዲሁም የአወሊያ መስጊድ ኢማም የሆኑት ሼክ ይማም ተባረዋል” ስትል አንዲት ስሟ እንዳይጠቀስ የፈለገች የአረቢኛ ቋንቋ የኮሊጅ ተማሪ ገልጻለች።

የጸጥታ ሃይሎች የትምህርት ቤቱን ግቢ ከበዋል፤ እስካሁን ሰልፉን ለመበተን ከማስፈራራት በስተቀር በተማሪዎቹ ላይ የደረሰባቸው ጥቃት የለም።

በወለጋ ዩኒቨርስቲ ደግሞ ተማሪዎች የምግብ ጥራት መጓደል አሳስቧቸዋል፤ አልፎም ለተቃውሞ አድርሷቸዋል።

ከለት ወደለት የደፈረሰ የጎርፍ ውሃ የመሰለ ሽሮ መብላት ታከተን፤ በአግባቡ ያልተበጠረና አሸዋ ያለበት እንጀራ መብላት እስከመቼ? የሚመደብልን በጀት በቂ ሆኖ ሳለ፤ የምግብ ጥራት ማሽቆልቆሉ ለምን? እያሉ ውስጥ ውስጡን ሲያጉተመትሙ የነበሩት የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች፤ የገና ለት ነው አንጀታቸው ለይቶለት የተቆረጠው።

ከቤተሰባቸው ተለይተው በዓሉን የሚያከብሩት ተማሪዎች እልቅ ቅጠል የማይል ምግብ ቀረበልን ሲሉ፤ ምግብ ላለምብላት ይወስኑና፤ በምግብ ቤቱ ዙሪያ ይሰባሰባሉ።

ተማሪዎቹ የምግብ ጥራት እንዲሻሻል ሲጠይቁ የመጀመሪያቸው አልነበረም። ወዲያውኑ የጸጥታ ሃይሎች በአካባቢው ተገኝተው ተማሪዎቹ ጋር ግብ ግብ ይገጥማሉ።

የታጠቁ ሃሎች በከፈቱት ተኩስ አንድ ተማሪ መቁሰሉንና ሌሎች ደግሞ መደብደባቸውን ተማሪዎቹ ይናገራሉ።

ጥቃት ከደረሰባቸው አንዱ በአሁኑ ወቅት የቀዶ ጥገና ህክምና ተደርጎለት በነቀምት ሆስቲታል ውስጥ ይገኛል።

የፌዴራልና የኦሮሚያ ፖሊስ በአካባቢው ተገኝተው በወሰዷቸው እርምጃዎች ድብደባ ደርሶባቸው በሆስፖታል የሚገኙ ተማሪዎች እንዳሉም ተገልጿል።

የሶስተኛ አመት ተማሪ ተስፋየ ደገፋ በአካዳሚክ ፕሬዝደንቱ ዶር ኤባ ሚጀና ስለተደበደብ ለህይወቱ አስጊ ሁኔታ ላይ እንደሚገን ተማሪዎቹ ለኦሮሚኛ ዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል።

የተማሪው የጤና ሁኔታ አስጊ በመሆኑ ለተጨማሪ የህክምና እርዳታ ወደ አዲስ አበባ ከአቅም በላይ ተብሎ ሊላክ እንደታሰበ ተማሪዎቹ ይናገራሉ።

በወለጋ ዩኒቨርስቲ የትምህርት ሂደቱ በከፊል ቀጥሏል። የዩኒቨርስቲውን ፕሬዝደንት ፕሮፌሰር ፈቃዱ በየነ የዝግጅት ክፍላችን በተደጋጋሚ ደውሎላቸው ስልካቸውን አያነሱም።

የምስራቅ ወለጋ የፖሊስ ኮሚሽነር ኢንስፔክተር ኦላና ጌታቸው የተጎዱ የሚባሉት ተማሪዎች ማን እንደደበደባቸውና ጥቃቱን እያደረሰባቸው እንደሆነ አልታወቀም ብለዋል።

እስካሁን የታሰሩ ተማሪዎች አለመኖራቸውን ነው ኢንስፔክተር ኦላና የገልጹት።

በደቡብ ክልል ሃዲያ ዞን ደግሞ፤ በሆሳእና ከተማና አካባቢዋ የሚገኙ ከ429 በላይ ተማሪዎች ትምህርታችንን አጠናቀን ስራ አጥተናል በሚል የዞኑ መስተዳድር የስራ እድል እንዲከፍትላቸው ጠይቀዋል።

ተማሪዎቹ ተወካዮች መርጠው ከመስተዳድሩ ጋር ለረጅም ጊዜ ሲደራደሩና ሁኔታውን ሲከታተሉ መቆየታቸውን ነው የሚናገሩት። በስተመጨረሻ ተወካዮቻቸው ከዞኑ መስተዳድር ጋር ለመነጋገር ገብተው ባለመመለሳቸው ተቃውሞው መባባሱን አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የጠየቀ ተማሪ ገልጾልናል።

የሃዲያ ዞን የፖሲስ አዛዥ ኮማንደር አዲሴ ፈይሳ ግጭቱ መፈጠሩን ገልጸው፤ ከታሰሩ ተማሪዎች መካከል ሁሉም ትምህርት ተሰጥቷቸው መፈታታቸውን ተናግረዋል።

XS
SM
MD
LG