የአሜሪካ እና የሩሲያ ከፍተኛ ባለሥልጣናት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት ስለሚሻሻልበት እና የዩክሬንን ጦርነት በማስቆም ላይ ያተኮረ ድርድር ለማድረግ ነገ ማክሰኞ ሳዑዲ አረቢያ ላይ ውይይት እንደሚያደርጉ ክሬምሊን አስታውቃለች፡፡
ሩሲያ ከሦስት ዓመታት በፊት ዩክሬንን ከወረረች ወዲህ በሁለቱ ሀገራት መካከል የሚደረግ ከፍተኛ ውይይት እንደኾነ ተነግሯል።
ውይይቱ የዶናልድ ትረምፕ አስተዳደር በሩሲያ ላይ የነበረውን የማግለል ፖሊሲ ለመቀልበስ የሚወስዱት ርምጃ ዋና አካል ተደርጎም ታይቷል።
ውይይቱ በአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትረምፕ እና በሩሲያው አቻቸው ቭላድሚር ፑቲን መካከል ለሚደረግ ስብሰባ ጥርጊያ መንገድ ለመክፈት ያለመ እንደኾነም ተመልክቷል።
የሁለቱ ሀገራት ስብሰባ መታቀዱ፣ ዩክሬንና የአሜሪካ አጋሮች በጠረጴዛ ውይይቱ ላይ ለመሳተፍ እንዲሯሯጡ አድርጓል የሚለው የአሶስዬትድ ፕረስ ዘገባ፣ ፈረንሣይ ከአውሮፓ ኅብረት አባል ሃገራት ጋራ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲደረግ ጥሪ ስታደርግ፣ እንግሊዝ ደግሞ በጉዳዩ ላይ ያላትን ውሳኔ ዛሬ እንደምታስታውቅ ይጠበቃል።
የሩሲያው የውጪ ጉዳይ ምኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ እና የውጪ ጉዳዮች አማካሪው ዩሪ ኡሻኮቭ ወደ ሳዑዲ መዲና ዛሬ እንደሚያቀኑ የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ አስታውቀዋል።
መድረክ / ፎረም