የደቡብ ኮሪያው ፕሬዝዳንት ዩን ሱክ ዮል የጸጥታ ሃላፊ የፖለቲካ ቀውሱን ወደ ሌላ ከፍተኛ ግጭት ሊገፋው ይችላል ባሉት የተከሰሱትን መሪ በቁጥጥር ስር ለማዋል ከሚደረገው ጥረት ጋር መተባበር እንደማይችሉ ዛሬ እሁድ ተናግረዋል፡፡
የእስር ትዕዛዙ ቀነ ገደብ ነገ ሰኞ እኩለ ሌሊት ላይ የሚጠናቀቅ ሲሆን የጸጥታ ሃላፊው ፓርክ ቾንግ-ጁን በትብብር ማዘዣው ዙሪያ ያለውን የሕግ ክርክርም ላለመተባበራቸው ምክንያት አድርገው ጠቅሰዋል።
አስተያየቶቹ የተሰጡት የሴኡል ፍርድ ቤት የእስር ማዘዣው ህገወጥ እና ልክ ያልሆነ ነው በማለት የፕሬዘዳንቱ ጠበቆች ያቀረቡትን ቅሬታ ውድቅ ካደረገ በኋላ ነው ሲሉ የደቡብ ኮርያ ሚድያዎች መዘገባቸውን የጠቀሰው ሮይተርስ ተጨማሪ አስተያየት ለመጠየቅ ወደ ፍርድ ቤት ያደረገው የስልክ ጥሪም ምላሽ እንዳላገኘም ገልጿል፡፡
ዮን እአአ ታህሳስ 3 ቀን ማርሻል ህግን ለማወጅ ባደረጉት ያልተሳካ ሙከራ ምክንያት በቁጥጥር ስር እንዲውሉ የእስር ትዕዛዝ የወጣባቸው የመጀመሪያው የደቡብ ኮሪያ ፕሬዚደንት ሆነዋል፡፡ ይህም በእስያ ባለአራተኛዋ ትልቅ ኢኮኖሚዋና የአሜሪካ ቁልፍ አጋር በሆነችው ደቡብ ኮርያ የውስጥ የፖለቲካ ትርምስ ቀስቅሷል፡፡
የዩናትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ከሃገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ለመነጋገር ዛሬ እሁድ ሴኡል ይደርሳሉ ተብሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዋና ከተማይቱ ሴኡል ከባድ በረዶ ባለበት በፕሬዘዳንት ዮን መኖሪያ አካባቢ በሺዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች ባደረጉት ሰልፍ የእስር ማዘዣው ውዝግብ ፈጥሯል፡፡
የተወሰኑ ሰልፈኞች ፕሬዘዳንቱ እንዲታሰሩ ሲጠይቁ ሌሎች ሰልፈኞች ደግሞ እስሩን ተቃውመው ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
መድረክ / ፎረም