በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የእስራኤል ታንኮች ወደ ሰሜንና ደቡብ ጋዛ አካባቢዎች እየገሰገሱ ነው


ፎቶ ፋይል - የእስራኤል ጦር ታንኮች በዋዲ ጋዛ፣ ማዕከላዊ ጋዛ ሰርጥ እንደ አውሮፓውያን የቀን አቆጣጠር ሰኔ 26፣ 2024 ዓ.ም.
ፎቶ ፋይል - የእስራኤል ጦር ታንኮች በዋዲ ጋዛ፣ ማዕከላዊ ጋዛ ሰርጥ እንደ አውሮፓውያን የቀን አቆጣጠር ሰኔ 26፣ 2024 ዓ.ም.

ዛሬ እሑድ፣ ሰኔ 23 ቀን 2016 ዓ.ም.፣ በሰሜናዊ ጋዛ ወደሚገኘው ሸጃያ ሰፈር የዘለቁት የእስራኤል ወታደሮች፣ ወደ ደቡብ ምዕራብ እና ማእከላዊ ራፋሕ በጥልቀት በመግባት፣ በትንሹ ስድስት ፍልስጥኤማውያንን ገድለው በርካታ ቤቶችን ማውደማቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ።

ከአራት ቀናት በፊት ወደ ሸጃያ የተመለሱት የእስራኤል ታንኮች፣ በብዙ መኖሪያ ቤቶች ላይ አነጣጥረው በመተኮሳቸው፣ ነዋሪዎች በየቤታቸው ታግተው ለመውጣት እንዳልቻሉ ገልጸዋል።

የእስራኤል ጦር፣ ባለፉት ቀናት በሼጃያ በሚንቀሳቀሱ ኀይሎች ላይ ወሰድኹት ባለው ርምጃ፣ ብዙ ፍልስጥኤማውያን ታጣቂዎችን መገደላቸውን፣ በርካታ የጦር መሣሪያዎችን ማግኘቱንና ወታደራዊ መሠረተ ልማቶችንም ማውደሙን አስታውቋል። ትላንት ቅዳሜ፣ በሰሜናዊ ጋዛ ሁለት እስራኤላውያን ወታደሮች መሞታቸውንም የአገሪቱ ጦር ሳይገልጽ አላለፈም።

ታጣቂው የሐማስ ክንፍ እና ተባባሪው እስላማዊ ጂሃድ፣ በሼጃያ እና ራፋህ ከፍተኛ ውጊያ መደረጉን አረጋግጠው፣ ተዋጊዎቻቸው እዚያ በሚንቀሳቀሱት የእስራኤል ወታደሮች ላይ፣ ፀረ ታንክ ሮኬቶችንና የሞርታር ቦምቦችን መተኮሳቸውን ተናግረዋል።

የእስራኤል ጦር፣ ከወራት በፊት ተቆጣጥሬአቸዋለኹ ባላቸው የጋዛ አካባቢዎች በሚገኙ ኀይሎቹ ላይ፣ ታጣቂዎቹ ጥቃት መሰንዘራቸውን ቀጥለዋል።

በዩናይትድ ስቴትስ የሚደገፉት የአረብ ሸምጋዮች ተነሣሽነቶች፣ እስከ አሁን የተኩስ አቁም ስምምነትን ለማምጣት አልቻሉም። የሐማስ ታጣቂ፣ ማንኛውም ስምምነት፣ ጦርነቱን ማስቆምና እስራኤላውያን ከጋዛ ሙሉ በሙሉ እንዲወጡ ማስቻል እንዳለበት ይናገራል፡፡ እስራኤል በበኩሏ፣ እ.ኤ.አ. ከ2007 ጀምሮ ጋዛን የሚያስተዳድረው ሐማስ እስካልጠፋ ድረስ፣ ጦርነቱን ለማቆም የምትስማማው በጊዜያዊነት እንደኾነ ገልጻለች።

በራፋሕ ከተማ ጥቃት የደረሰው ሞት

የግብጽ ደንበርተኛ በኾነችው ራፋሕ ከተማ፣ የእስራኤል ታንኮች፥ በምሥራቅ፣ በምዕራብ እና በከተማዪቱ መሀል ወደሚገኙ በርካታ ወረዳዎች ዘልቀው ገብተው፣ ሻቦራ በተሰኙት መኖሪያ ቤቶች ላይ ባደረሱት ጥቃት ሰዎች መሞታቸውን የሕክምና ባለሞያዎች ተናግረዋል።

ስድስቱ የዙሩብ ቤተሰብ አስከሬኖች፣ በአቅራቢያው የካን ዮኒስ ከተማ ወደሚገኘው ናስር ሆስፒታል ተወስዷል። ዛሬ እሑድ፣ ከ12 በላይ የተቆጠሩ የቤተሰቡ ዘመዶች፣ በነጭ መሸፈኛዎች በተጠቀለሉት አስከሬኖች ፊት ቆመው ሐዘናቸውን በመግለጽ ወደተዘጋጁ መቃብሮች ወስደዋቸዋል።

የእስራኤል ጦር፣ በራፋሕ ከተማ መሀል የሚገኘውን በጣም ታዋቂውን የአል-አውዳ መስጅድ ማቃጠሉን ነዋሪዎች አመልክተዋል።

እስራኤል፣ የራፋሕ ወታደራዊ ዘመቻዋ፣ የሐማስ ታጣቂን የመጨረሻ ሻለቃ ጦር ለማጥፋት የምታካሒደው እንደኾነ አስረድታለች። በራፋሕ ውስጥ “ዒላማ የተደረገ፣ በመረጃ ላይ የተመሠረተ” ዘመቻ መቀጠሉን ያመለከተው የእስራኤል ጦር፣ በተለያዩ ውጊያዎች በርካታ ታጣቂዎችን መግደሉንና ዋሻዎችን ማፍረሱን ገልጿል።

የጋዛው ጦርነት፣ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ጥቅምት 7 ቀን 2024 የተቀሰቀሰው፥ በሐማስ የሚመሩ ታጣቂዎች ደቡብ እስራኤልን በመውረር፣ 1ሺሕ200 የሚጠጉ ሰዎችን ሲገድሉ፣ ከ250 በላይ ታጋቾችን ደግሞ በያዙበት ወቅት ነው።

እስራኤል በአጸፋው በወሰደቸው የበቀል ጥቃት፣ እስከ አሁን፣ 38ሺሕ የሚደርሱ ሰዎች መገደላቸውን፣ በሐማስ የሚመራው የጋዛ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ገልጾ፣ በከፍተኛ ደረጃ የተገነባው የባሕር ዳርቻ አካባቢም መፍረሱን አመልክቷል።

ሚኒስቴሩ፣ ተዋጊ እና ተዋጊ ያልኾኑ ሟቾችን ቁጥር ለይቶ ባያስቀምጥም፣ ባለሥልጣናቱ ግን ከሟቾቹ የሚበዙት ሲቪሎች መኾናቸውን አስታውቀዋል።

እስራኤል በበኩሏ፣ በጋዛ ከ300 በላይ ወታደሮቿ መሞታቸውን ስትገልጽ፣ በእስከ አሁኑ ጥቃቷ ከፍልስጥኤም ታጣቂዎች አንድ ሦስተኛ የሚኾኑ ተዋጊዎችን መግደሏን ተናግራለች።

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG