በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

መንግሥት ከፋኖ ታጣቂ ጋራ ቀጥተኛ ውይይት እንዲያደርግ ተጠየቀ


መንግሥት ከፋኖ ታጣቂ ጋራ ቀጥተኛ ውይይት እንዲያደርግ ተጠየቀ
please wait

No media source currently available

0:00 0:07:17 0:00

ከኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት እና የክልል ርእሳነ መስተዳድሮች ጋራ የተወያዩት የአማራ ክልል ከተሞች ነዋሪዎች፣ መንግሥት ከፋኖ ታጣቂዎች ጋራ ቀጥተኛ ውይይት ቢያደርግ የተሻለ ሰላም ሊመጣ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡

ባለሥልጣናቱ፣ ከክልሉ የ15 ከተሞች ነዋሪዎች ጋራ፣ ትላንት እሑድ በወቅታዊው የክልሉ የጸጥታ ችግሮች ላይ ተወያይተዋል። ውይይቶቹን በበጎ እንደሚመለከቷቸው የገለጹ የአሜሪካ ድምፅ ያነጋገራቸው ተሳታፊዎች፣ ሆኖም፣ “ከታጣቂ ቡድኑ ጋራ ቀጥተኛ ውይይት ቢደረግ የተሻለ ሰላምን ያመጣል፤” ብለዋል።

ውይይቶቹ የተካሔዱት፣ በክልሉ የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፣ ለተጨማሪ አራት ወራት ከተራዘመ ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

ነዋሪዎቹን ያወያዩት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በበኩላቸው፣ የአማራ ሕዝብ ችግሮችን እንደተረዱ ጠቅሰው፣ ለመፍትሔዎቹም እንደሚሠሩ ተናግረዋል፡፡

የባሕር ዳሩን መድረክ የመሩት የሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር ሙስጠፌ መሐመድ፣ “ጥያቄዎችን በመሣሪያ ለመፍታት ማሰብ የችግሮቻችን ሁሉ ምንጭ ነው፤” ማለታቸውን የመንግሥት ብዙኀን መገናኛዎች ዘግበዋል።

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ትምህርት ክፍል ረዳት ፕሮፌሰር ያያው ገነት ቸኮል፣ መንግሥት ሕዝባዊ ውይይቶችን ማመቻቸቱ የተሻለ የሰላም አማራጭ እንደሚያመጣ ጠቁመው፣ ከታጣቂ ቡድኑ ጋራ ፊት ለፊት መነጋገር ግን “የተሻለው መንገድ” እንደሆነ በነዋሪዎቹ የተገለጸውን አጠናክረዋል።

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ይከታተሉ።

XS
SM
MD
LG