በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የዝንጀሮ ፈንጣጣ ኮንጎ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በግብረ-ስጋ ግንኙነት መዛመቱን የዓለም ጤና ድርጅት አስታወቀ


ምስሉ በማቀዝቀዣ ውስጥ የተቀመጡ የዝንጀሮ ፈንጣጣ ክትባት ጠርሙሶችን ያሳያል
ምስሉ በማቀዝቀዣ ውስጥ የተቀመጡ የዝንጀሮ ፈንጣጣ ክትባት ጠርሙሶችን ያሳያል

ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ግዙፍ የተባለ ወረርሽኝ ጋር በመጋፈጥ ላይ ባለችበት በአሁኑ ሰዓት ፣ ፣ የዓለም የጤና ድርጅት የዝንጀሮ ፈንጣጣ በመባል የሚጠራው በሽታ ሀገሪቱ ውስጥ በግብረ ሥጋ ግንኙነት መተላለፉን ለመጀመሪያ ጊዜ አረጋግጫለሁ ሲል አስታውቋል ። ይሄም በሽታውን ለማስቆም የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ ሊያከብደው እንደሚችል የአፍሪካ ተመራማሪዎች አስታውቀዋል ።

የጤናው ድርጅት ሀሙስ ምሽቱን ባወጣው መግለጫ ፣ በመጋቢት ወር ወደ ኮንጎ ያቀና አንድ የቤልጂየም ዜጋ የዝንጀሮ ፈንጣጣ እንደተገኘበት ይፋ አድርጓል ። ግለሰቡ ፣ ከሌሎች ወንዶች ጋር የወሲብ ግንኙነት ያለው መሆኑን እንዲሁም ወደ ተለያዩ ድብቅ የተመሳሳይ ጾታ እና ከሁለቱም ጾታዎች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሰዎች መዝናኛ ስፍራዎችን ይሄድ እንደነበረ ድርጅቱ አስታውቋል ። ከግለሰቡ ጋር ግንኙት የነበራቸው 5 ሰዎች በሽታው እንደተገኘባቸው ድርጅቱ አክሏል ።

"ይህ በአፍሪካ የዝንጀሮ ፈንጣጣ በሽታ በግብረ ሥጋ ግንኙነት የመተላለፉ የመጀመሪያው ትክክለኛ ማረጋገጫ ነው" ብለዋል - በተለያዩ የዓለም ጤና ድርጅት አማካሪ ቡድኖች ውስጥ አባል የሆኑት ናይጄሪያዊው ከቫይረስ ጋር የተገናኙ በሽታዎች አጥኚ ኦይዋሊ ቶሞሪ ። "ይህ ዓይነቱ ስርጭት እዚህ ሊከሰት አይችልም የሚለው ሀሳብ አሁን ውድቅ ሆኗል ።" ሲሉም አክለዋል ።

የዝንጀሮ ፈንጣጣ (ኤምፖክስ ) በመካከለኛው እና ምዕራብ አፍሪካ ክፍሎች ለብዙ አሥርተ ዓመታት የተስፋፋ ሲሆን በአብዛኛው በበሽታው ከተያዙ አይጦች ወደ ሰዎች በመዛመት ውስን ወረርሽኞችን አስከትሏል።

ባለፈው ዓመት ፣ በዋነኝነት አውሮፓ ውስጥ ከተመሳሳይ ጾታ እንዲሁም ከሁለቱም ጾታዎች ጋር ግንኙነት ባላቸው ወንዶች ላይ የተከሰተው በሽታ ከ 100 በላይ አገሮችን አጥቅቷል። የዓለም ጤና ድርጅት ወረርሽኙን እንደ ዓለም አቀፍ ድንገተኛ አደጋ ያወጀ ሲሆን እስካሁንም ወደ 91,000 የሚጠጉ ሰዎች ላይ መከሰቱ ተነግሯል ።(ዘገባው የሶሼትድ ፕረስ ነው ።)

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG