በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በአዋሽ አርባ ታስረው የቆዩ የትግራይ ተወላጅ የመከላከያ አባላት እንደተፈቱ ተገለጸ


በአዋሽ አርባ ታስረው የቆዩ የትግራይ ተወላጅ የመከላከያ አባላት እንደተፈቱ ተገለጸ
please wait

No media source currently available

0:00 0:10:31 0:00

በትግራይ ክልል ከተጀመረው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ጋራ በተገናኘ፣ በግንቦት ወር 2013 ዓ.ም. ላይ ተይዘው ላለፉት ሦስት ዓመታት፣ “ዐዲስ ራዕይ” በሚባል ወታደራዊ ማሠልጠኛ ካምፕ ታስረው የቆዩ፣ 32 የትግራይ ተወላጅ የመከላከያ ሠራዊት አባላት፣ ባለፈው ሳምንት እንደተፈቱ ገለጹ።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁን አስተያየት ሰጭዎች፣ አዋሽ አርባ አካባቢ ወደሚገኘው ወታደራዊ ማሠልጠኛ ካምፕ ተወስደው፣ “ከመከላከያ ሠራዊት ኮብልላችኋል” የሚል ክሥ ቀርቦባቸው እንደተፈረደባቸው ገልጸዋል፡፡ ታስረው በቆዩባቸው ዓመታት፣ የተለያዩ የመብቶች ጥሰት እንደተፈጸሙባቸው አውስተው፣ አሁንም፣ “ያለምንም ድጋፍ አውጥተው በትነውናል፤” ብለዋል፡፡

ክሥ ሳይመሠረትባቸው የታሰሩ ቀሪ ስድስት ጓዶቻቸው፣ በዚያው ካምፕ ውስጥ፣ ለረኀብ እና ለበሽታ ተጋልጠው እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ በካምፑ አብረዋቸው ከነበሩ እስረኞች መካከልም፣ የተወሰኑት ተለይተው እንደተወሰዱና እስከ አሁን የት እንዳሉ እንደማያውቁም አመልክተዋል፡፡

በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የታሰሩ የትግራይ ተወላጆችን ኹኔታ እንደሚከታተል የገለጸው ሂዩማን ራይትስ ፈርስት የተባለ ኢትዮጵያዊ የመብቶች ተሟጋች ድርጅት በበኩሉ፣ በፕሪቶርያው ስምምነት መሠረት፣ ሁሉም እስረኞች እንዲለቀቁ በድጋሚ ጥሪ አቅርቧል፡፡

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደርም ቀደም ብሎ እንዳስታወቀው፣ በፕሪቶርያው በተደረሰው የሰላም ስምምነት መሠረት ካልተፈጸሙት ነገሮች አንዱ፣ እስረኞችን ካለመፍታት ጋራ የሚያያዝ ነው፡፡ ስለ ጉዳዩ፣ ከፌዴራሉ መንግሥት ጋራ ሁልጊዜ ውይይት እንደሚደረግም፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ አክሎ መግለጹ ይታወሳል፡፡

/ዘገባው በአሜሪካ ድምፅ ዘጋቢዎች የተሰናዳ ነው። ኤደን ገረመው በድምፅ አንብባዋለች/

XS
SM
MD
LG