በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የቡርኪናፋሶ ወታደሮች ሕፃናትን መረሸናቸው ተረጋገጠ


የቡርኪናፋሶ ወታደሮች ሕፃናትን መረሸናቸው ተረጋገጠ
please wait

No media source currently available

0:00 0:06:10 0:00

· በወታደራዊ ካምፕ የተቀረፀው ቪዲዮ ይፋ ኾኗል

በቡርኪናፋሶ፣ በወርኀ የካቲት አጋማሽ፣ በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ የተለቀቀውና ወታደራዊ መለዮ የለበሱ ሰዎች፣ በሕፃናት አስከሬን መሀከል ሲዘዋወሩ የሚያሳየው ምስል፣ በወታደራዊ ካምፕ ውስጥ መቀረፁን አሶሽየትድ ፕሬስ ያደረገው ማጣራት አረጋግጧል። ከሟቾቹ የአንዱን ቤተሰብም አግኝቶ አነጋግሯል።

የ16 ዓመቱ አዳማ፣ በሰሜን ቡርኪናፋሶ ከሚገኘው የአያቱ ቤት ብዙም ሳይ ርቅ ከሚገኝ ስፍራ የሚኖሩ ላሞቹን ለመመገብ፣ ለማይቆጠሩ ጊዜያት በእግሩ ተመላልሷል። በየካቲት ወር አጋማሽ አንድ ቀን ግን፣ ኢማም የመኾን ሕልም የነበረው ታዳጊ ወደ ቤቱ ሳይመለስ ቀረ።

አዳማ ደብዛው ከጠፋ ከቀናት በኋላ ቤተሰቦቹ ያዩት፣ በሞባይል ስልክ አማካይነት ሲሠራጭ በነበረ አሠቃቂ የቪዲዮ ምስል ላይ ነበር። አዳማ እና ሌሎች ደማቸው የፈሰሰ ስድስት ልጆች፣ እጆቻቸው ታስረው፣ አብዛኞቹ እስከ ወገባቸው ራቁታቸውን ኾነው ወድቀው ይታያሉ።

በዙሪያቸው በደርዘን የሚቆጠሩ ሰዎች ከበዋቸው፣ አብዛኞቹ በድካም መንፈስ በሬሳዎቹ መካከል እየተረማመዱ፣ ሌሎቹ ደግሞ ቪዲዮ እየቀረፁ ይታያል።

በመሀል ከወታደሮቹ አንዱ እየሮጠ ወደ አዳማ በመሔድ ራስ ቅሉ ላይ ድንጋይ ሲያሳርፍበትም ይታያል፡፡ ከተሠነጠቀው የደረቀ ቁስል ደም ሲፈስ፣ ቪዲዮን የሚቀርፀው ሰው ደግሞ ሲሥቅ ይሰማል። “ይኼኛው አልሞተም ነበር፤” ይላል ሰውዬው ወደ አዳማ እያሳየ።

ለቤተሰቦቹ ደኅንነት ሲባል አሶስዬትድ ፕሬስ የአዳማን ሙሉ ስም ከመግለጽ ተቆጥቧል። ሰውዬውን ጨምሮ፣ “ለምንም አትጠቅሙም፡፡ ሰው ከመግደል ውጪ ሌላ ሥራ የላችኹም። ኹላችሁንም አንድ በአንድ እንገድላችኋለን፤” ይላል።

የቡርኪናፋሶ ጦር፣ በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት የጦር ወንጀል የኾነውን ይህን ግድያ “አልፈጸምኹም” ሲል ሓላፊነት እንደማይወስድ ገልጿል። ኾኖም፣ አሶስዬትድ ፕሬስ የተመለከተው 83 ሰከንድ ያህል ርዝማኔ ያለው ቪዲዮ እና ከሳተላይት የተገኙ ምስሎች፣ ግድያው አዳማ ከሚኖርበት አቅራቢያ፣ ኡአሂጉያ ከተሰኘ ከተማ በስተሰሜን ምዕራብ ኹለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ መፈጸሙን ያሳያሉ።

በቪዲዮ ላይ የለበሱትን ዩኒፎርም እና ተሽከርካሪዎቻቸውን በመመልከት፣ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ፣ በአሜሪካ እና በአውሮፓ ኅብረት የሥልጠና እና የትጥቅ ድጋፍ ይሰጣቸው የነበሩ፣ የቡርኪናፋሶ የጸጥታ ኃይል አባላት መኾናቸውን፣ አሶስዬትድ ፕረስ ገልጿል።

የአዳማ እናት፣ ልጃቸው በጸጥታ ኀይሎች መያዙን የሰሙት ከሌላ ዘመዳቸው ነው፡፡ እስከ አሁን ግን፣ መገደሉን የሚያሳየውን ምስል አልተመለከቱም፡፡ አዳማ ረጅም ዕድሜ የመኖር ዕድል ቢያገኝ ኖሮ፣ማኅበረሰቡ እንዲያድግ ይረዳ ነበር። አሁን ያ ዕድል የለውም። ሞቱን ከሰማኹበት ቀን አንሥቶ ኀዘን ላይ ነኝ፤ አለቅሳለኹ፤ ግን ምን ለውጥ አመጣለኹ፤ ምንም። እግዚአብሔር ነው የሰጠኝ፤ራሱ እግዚአብሔር መልሶ ወስዶታል። ምንም ማድረግ አንችልም። የሰው ልጅ ኹሉ ይህ ዕጣ ይገጥመዋል። ኹላችንም ሟቾች ነን፤ አንድ ቀን እንሞታለን።”

ላለፉት ሰባት ዓመታት፣ ቡርኪናፋሶ ከአልቃዒዳ እና ከእስላማዊ መንግሥት ቡድን ጋራ በተገናኘ በሁከት ስትናጥ ቆይታለች። መንግሥት፣ የሚደርሱትን ጥቃቶች ማቆም ባለመቻሉ፣ ባለፈው ዓመት ኹለት መፈንቅለ መንግሥቶች ተደርገዋል፤ ዐማፅያኑንም ለማጥፋት ቃል ቢገቡም፣ ብዙም የተቀየረ ነገር የለም። ይልቁንም ቡርኪናፋሶ፣ አፍጋኒስታንን በመተካት፣ በዓለም ደረጃ በአክራሪዎች ጥቃት ከፍተኛ ሞት የተመዘገበባት ሀገር መኾኗን፣ ዓለም አቀፉ ሽብር ጠቋሚ ተቋም ያወጣው ሪፖርት አመልክቷል።

አክራሪዎቹ ከሚያደርሱት ጥቃት በላይ ነዋሪዎች የበለጠ የሚፈሩት፣ ከፍርድ ቤት ዕውቅና ውጪ ግድያ የሚፈጽሙትንና ዐማፅያኑን ትደግፋላችኹ፤ በሚል ቁጥራቸው ለማይታወቅ በርካታ ሰዎች መጥፋት ምክንያት የኾኑትን የቡርኪናፋሶ የጸጥታ ኃይሎች እንደኾነ ይናገራሉ፤ “አንድ ቀን አድማ በመንገድ ላይ ዝም ብሎ እንዳይዘዋወር ነገርኹት። መንገድ ላይ መዘዋወር አደገኛ ነው፤ ሰዎች የአክራሪዎቹ አባል አርገው ሊቆጥሩኽ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ፣ ከአያትኽ ቤት ብዙ አትራቅ ብዬው ነበር። እዚያው ዐርፈኽ ቆይና እግዚአብሔር ሲፈቅድ እጎበኝሃለኹ፤ አልኹት። እግዚአብሔር ሲፈቅድ ሔጄ ላየውና ወደ ቤት ስመለስ ይዠው ልመጣ ነበር፡፡”

አዳማ ከተሰወረ ከቀናት በኋላ፣ አስከሬኑ፣ ቪዲዮው በተቀረጸበት ወታደራዊ ጣቢያ አቅራቢያ መንገድ ዳር ወድቆ ተገኘ። አሶስዬትድ ፕሬስ ያነጋገረው የአዳማ አጎት፣ የእህቱን ልጅ አስከሬን ሲያይ የተሰማውን እንዲህ ይገልጻል፤ “ምስሉን ስመለከት አዳማ መኾኑን አምኜ መቀበል አልፈለግኹም ነበር። ነገር ግን አውቄዋለኹ። እውነቱን ለመናገር፣ በጣም ነበር ያዘንኹት። በርግጥ፣ የሰው ልጅ ኹሉ ይሞታል፤ በእንደዚኽ ዐይነት አሠቃቂ አሟሟት ግን በእጅጉ ነው ያዘነው። ምንም ማድረግ የምንችለው ነገር የለም።”

በቡርኪናፋሶ የሚደርሰው ጥቃት፣ በተወላጅነት ማንነት ላይ ያነጣጠረና በተለይ የፉላኒ

ብሔር ተወላጆች ሕፃናትን ጨምሮ ዒላማ እየተደረጉ መምጣታቸውን፣ በአካባቢው የመብት

አቀንቃኝ ቡድን የኾነው ተቋም ዋና ጸሐፊ ዳውዳ ዲያሎ ይገልጻሉ።

“ሕፃናትን እየጎዳ ያለው የጸጥታ ጉዳይ ያሳስበናል። በተለያዩ እንቅስቃሴዎች ወቅት፣ የጸጥታ ኃይሉ አባላት፣ ሕፃናትን ጠልፈው መውሰዳቸው ዐዲስ አይደለም። ሕፃናት ከብት ሲጠብቁ ታፍነው ከፍተኛ ጥበቃ ወደሚደረግበት እስር ቤት ይወሰዳሉ - የ10 ዓመት ዕድሜ ያላቸው ሕፃናት ሳይቀሩ። ይህ ሊታረም የሚገባ አሠራር ነው።”

ከእስላማዊ መንግሥት እና ከአልቃዒዳ ቡድኖች ጋራ የሚደረገውን ውጊያ ለማገዝ፣ ዩናይትድ ስቴትስ እና የአውሮፓ ኅብረት ለቡርኪናፋሶ በዐሥር ሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር የሚያወጣ ወታደራዊ ሥልጠና እና ቁስቁስ ሰጥተዋል።

የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ በአወጡት መግለጫ፣ በቪዲዮ ምስል የሚታየውን አሠቃቂ ጥቃት አውግዟል፡፡ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ውንጀላዎች ተጣርተው፣ የጥቃቱ ፈጻሚዎች ተጠያቂ ሊኾኑ ይገባል፤ ብለዋል።

የቡርኪናፋሶ መንግሥት ቃል አቀባይ፣ ለአሶስዬትድ ፕሬስ በሰጡት ምላሽ፣ ብዙ ጊዜ ታጣቂዎች የጸጥታ ኀይሎችን በመምሰል እና ተግባራቸውን በመቅረፅ፣ የፀጥታ ኀይሉን ተጠያቂ ለማድረግ ይሞክራሉ፤ ብለዋል፡፡ የግጭት ተንታኞች በበኩላቸው፣ ታጣቂዎች አብዛኛውን ጊዜ ለሚያደርሷቸው ጥቃቶች፣ የጸጥታ ኀይሎችን ተጠያቂ እንደማያደርጉና የአካባቢውን ሕዝብ በመፍራት ሕፃናትን እንደማይገድሉ ይገልጻሉ።

XS
SM
MD
LG