ፍልሰተኞችን አሳፍራ ወደ ጣሊያን በመጓዝ ላይ የነበረች አንዲት የእንጨት ጀልባ ባህር ዳርቻው ከመድረሷ በፊት በመበታተኗ አንድ ሕፃን ጨምሮ የ48 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የጣሊያን ባለሥልጣናት ተናገሩ። ሰማንያ የሚሆኑ ፍልሰተኞች ከአደጋው መትረፋቸውን ባለሥልጣናቱ ጨምረው ገልፀዋል።
በጣሊያን ግዛት ውስጥ በምትገኝ ክሮተን ከተማ ባህር ዳርቻ አቅራቢያ በሚገኝ የመዝናኛ ስፍራ በባህሩ ላይ ሕይወታቸው ያለፉ ሰዎች አስክሬን ዛሬ እሁድ መገኘቱን የከተማው ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። የከተማይቱ ከንቲባ ቪንሴንዞ ቮስ “ሁኔታው እጅግ በጣም አሳዛኝ ነው” ብለዋል።
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስትያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት አቡነ ፍራንሲስ፤ “ለጠፉትና በሕይወት ለተረፉት ለእያንዳንዳቸው ስደተኞች እፀልያለሁ” ብለዋል። አያይዘውም ስደተኞቹን ላተረፉና በሕይወት የተረፉትንም ለሚቀበሉ ፀሎት እያደረጉ እንደነበር ተናግረዋል።