ማሊ በሚዲያዎች ላይ የጣለችው እገዳ በቀጠናው ለሚዲያ ነፃነት ጥላቻ እያደገ መሄዱን ያሳያል ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ ኮሚሽነር ቢሮ አስጠነቀቀ።
የመንግስታት ድርጅቱ የሰብዓዊ መብት ባለስልጣናት ማሊ ረቡዕ እለት ዓለም አቀፉን ራዲዮ ፍራንስ እና ፍራንስ 24 የተሰኙትን ጣቢያዎች ማገዷ ትልቅ ድንጋጤ እንደፈጠረባቸው የገለፁ ሲሆን የተቋሙ ቃል አቀባይ ራቪና ሻምዳሳኒ በማሊ የሰፈነው ፍርሃት በጋዜጠኞች እና ጦማሪዎች ላይ ጫና እያሳደረ መሆኑን ገልፀዋል።
ሻምዳሳኒ በማሊ ዓለም አቀፎቹ የሰብዓዊ መብት እና ሰብዓዊነት ህግጋት በከፍተኛ ሁኔታ እየተጣሱ መሆኑን የሚያሳዩ ማስረጃዎች እየታዩ ነው ያሉ ሲሆን ተጨማሪ ምርመራዎች ሊደረጉ እንደሚገባም ተናግረዋል።
በዓለም ዙሪያ በጋዜጠኞች ላይ የሚደርሱ ማስፈራራቶች እየጨመሩ መሄዳቸውን ያመለከቱት ሻምዳሳኒ መንግስታት ጋዜጠኞችን ለማዋከብ እና ነፃ የመረጃ ዝውውርን ለመገደብ እንደመሳሪያ የሚጠቀሙባቸው በርካታ መንገዶች እንዳላቸውም ጨምረው አብራርተዋል።