በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የትግራይ ኃይሎች በአማራ ክልል በቆቦና በጭና የፈፀሙት ጥቃት “በሰብዓዊነት ላይ የተፈፀመ እና የጦር ወንጀል ሊሆን ይችላል”ሲል አምነስቲ አስታወቀ


ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የትግራይ ኃይሎች ሲል የጠራቸው ታጣቂዎች በሰሜን ወሎና ሰሜን ጎንደር ዞኖች የተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ባወጣበት ሪፖርት ላይ የተጠቀማቸው ምስሎች
ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የትግራይ ኃይሎች ሲል የጠራቸው ታጣቂዎች በሰሜን ወሎና ሰሜን ጎንደር ዞኖች የተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ባወጣበት ሪፖርት ላይ የተጠቀማቸው ምስሎች

ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የትግራይ ኃይሎች ሲል የጠራቸው ታጣቂዎች በአማራ ክልል ሰሜን ወሎና ሰሜን ጎንደር ዞኖች በነበሩበት ወቅት በተለይም በቆቦና የተወሰኑ የጭና አካባቢዎች የተፈፀሙ የሰብዓዊ መብትጥሰቶችን መርምሮ ሪፖርት ማውጣቱን አስታውቋል።

አምነስቲ ዛሬ በወጣው አዲስ ሪፖርት፣ በሁለቱ አካባቢዎች “ከህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ጋር ግንኙነት ያላቸው ታጣቂዎች፣ ሆን ብለው በደርዘን የሚቆጠሩ ሰዎችን ገድለዋል፤ እድሜያቸወ 14 ዓመት የሆኑትን ጨምሮ በደርዘን የሚቆጠሩ ሴቶችን እና ልጃገረዶችን በቡድን ደፍረዋል፤ የግል እና የህዝብ ንብረቶችን ዘርፈዋል” ብሏል፡፡

በጭና እና ቆቦ አከባቢዎች የጭካኔ ድርጊቶቸ የተፈፀሙት፣ የትግራይ ሃይሎች በሐምሌ ወር 2013 ዓ.ም አካባቢዎቹን ከተቆጣጠሩ ብዙም ሳይቆይ በነሀሴ ወር መጨረሻ እና በመስከረም መጀመሪያ እንደነበር አምነስቲ አስታውቋል፡፡ በጭካኔ ከተሞሉ ጥቃቶቸ በተጨማሪ የግድያ ዛቻዎች እና ማንነትን መሰረት ያደረጉ ስድቦች እና አዋራጅ ተግባራትም ይፈጸሙ እንደነበር ሪፖርቱ አመልክቷል።

በቆቦ የትግራይ ሃይሎቸ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የጭካኔ ተግባራትን የፈጸሙት፣ የአካባቢው ሚሊሻዎች እና ታጣቂዎች በከፍተኛ መጠን በመከላከላቸው ምክንያት በወሰዱት የበቀል እርምጃ እንደሚመስል የአምነስቲ ሪፖርት ጠቅሷል፡፡

የድርጅቱ የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች አጥኒ አቶ ፍሰሃ ተክሌ ስለ ሪፖርቱ ለአሜሪካ ድምጽ ሲያብራሩ "በቆቦ ከተማ እና አካባቢው ጳጉሜ 4 እ 5 2013 ዓ.ም በርካታ ሰላማዊ ሰዎች፣ በተለይ በከተማው፣ በትግራይ ሃይሎች ተገድለዋል" ብለዋል፡፡ "በጭና አካባቢ ደግሞ፣ ሐምሌ እና ነሐሴ ላይ ቤት ውስጥ የተገኙ ሴቶች አሰቃቂ የሆነ ጾታዊ ጥቃት፣ በተለይም 18 ዓመት ያልሞላቸውን ሴቶች ጨምሮ በቡድን ለተራዘመ ጊዜ አስገድዶ መድፈር በህወሃት ሃይሎች ተፈጽሞባቸዋል" ሲሉም አክለዋል፡፡

በሁለቱም አካባቢዎች የተፈጸሙት ግድያዎች እና የአስገድዶ መድፈር ተግባራት በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል እንዲሁም የጦር ወንጀል ሊሆን እንደሚችልም አቶ ፍሰሃ ተክሌ ገልጸዋል፡፡

በአምነስቲ ኢንተርናሽናል የምስራቅ አፍሪካ እና ታላላቅ ሀይቆች አካባቢ ምክትል ዳይሬክተር ሳራ ጃክሰን ደግሞ "የትግራይ ሃይሎች ሁሉም ተፋላሚ ወገኖች ሊከተሏቸው ለሚገቡት መሰረታዊ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ህግ ደንቦች ፍጹም ቸልተኝነት አሳይተዋል" ማለታቸው በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡ ምክትል ዳይሬክተሯ አክለውመ "ከሐምሌ 2013 ዓ.ም ጀምሮ የትግራይ ሃይሎች በአማራ ክልል በሚገኙ አካባቢዎች የጦር ወንጀል እና በሰው ልጆች ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለመፈጸማቸው የሚያሳዩ መረጃዎች እየጨመሩ ነው።

ይህም በብዛት የሚስተዋለውን ተደጋጋሚ የአስገድዶ መድፈር ክስተት፣ የጅምላ ግድያ እና ከሆስፒታሎች ጭምር የተፈተመ ዘረፋን ይጨምራል” ሲሉ ተናግረዋል።

አምነስቲ ምርመራ ባደረገባቸው በቆቦ እና ጭና አካባቢዎች ተፈጽመዋል ስላላቸው የግድያ፣ አስገድዶ መድፈር እና የዘረፋ ተግባራት ከአካባቢው ነዋሪዎች አገኘሁ ያለውን ምስክርነትም በሪፖርቱ አካቷል፡፡

በሌላ በኩል ህወሓት በቀረበው ሪፖርት ላይ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ቀጥተኛ ምላሽ ያልሰጠ ሲሆን ከዚህ ቀደም መሪዎቹ በተለያየ ጊዜ በሰጧቸው ምላሾች፤ እንዲህ ዓይነት ከሰብዓዊ መብት ጥሰት ጋር በተያዙ የሚቀርቡ ውንጀላዎችን አይቀበሏቸውም።

ከዚህ ቀደም ክልሉን በፕሬዚደንትነት ማስተዳደር ላይ የሚገኙት ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረ ሚካኤል ‘የትግራይ ኃይሎች በአፋርና አማራ ክልሎች በሰላማዊ ዜጎች ጉዳት እያደረሱ ነው’ በሚል የሚሰነዘረውን ወቀሳ በማስተባበል፣ እንዲህ ወንጀል “የሰራዊቱ ባህሪና ተግባር እንዳልሆነ” ተናግረው ነበር።

ጉዳዩንም ገለልተኛ የሆኑ ዓለም አቀፍ ተቋማት እንዲመረምሯቸው ጥያቄ አቅርበው ነበር። በተጨማሪም ከትግራይ ክልል ባለሥልጣናት በኩል፣ እንዲህ ያሉ የመብት ጥሰቶች የተፈፀሙት ትግራይ ክልል ውስጥ መሆኑን በመጥቀስ እንዲህ ያሉ ሪፖርቶች በትግራይ ለተፈፀሙ ጥሰቶች ተመሳሳይ ትርክት ለመፍጠር የታለሙ እንደሆኑ ሲናገሩ ተሰምተዋል።

ሂውማን ራይትስ ዎች የተባለው ሌላው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅትምከሁለት ወራት በፊት ባወጣው የምርመራ ሪፖርት፣ በቆቦ እና በጭና አካባቢዎች በአጠቃላይ በትንሹ 97 ሰላማዊ ሰዎች በህወሓት ታጣቂዎች መገደላቸውን ከአካባቢው ነዋሪዎች ማረጋገጡን መግለጹ ይታወሳል፡፡

ይህ የግድያ ተግባር የጦር ወንጀል ሊሆን እንደሚችል የጠቆመው ድርጅቱ፣ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ምርመራ እንዲያደርግም በሪፖርቱ ምክረ-ሃሳብ አቅርቧል፡፡

/የአምነስቲ ኢንተርናሽናልን የዛሬ ሪፖርት በተመለከተ በምሽቱ የዜና ሰዓታችን ሰፋ ያለ ዘገባ እናቀርባለን፡፡/

XS
SM
MD
LG