በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በኢትዮጵያ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ እንዲካሄድ ግጭቶች መቆም አለባቸው


በኢትዮጵያ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ እንዲካሄድ ግጭቶች መቆም አለባቸው
please wait

No media source currently available

0:00 0:07:30 0:00

በኢትዮጵያ ከወራት በኃላ የሚደረገው ምርጫ ነፃና ገለልተኛ እንዲሆን በሀገሪቱ የተከሰቱ ግጭቶች ሊቆሙና ሰብዓዊ ርዳታ ለሚያስፈልጋቸው በአስቸኳይ ሊዳረስ እንደሚገባ በዩናይትድ ስቴትስ ምክር ቤት የውጪ ጉዳዮች ኮሚቴ አዲስ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ግሪጎሪ ሚክ ተናገሩ። ሚክ በቅርቡ ምርጫ ያካሄደችውን ዩጋንዳን ጨምሮ አሜሪካ ከአፍርካ አገሮች ጋር ትኩረት አርጋ ስለምትሰራባቸው ጉዳዮችም አብራርተዋል።

አዲሱ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ወደ ስልጣን ከመጡ በኃላ በምክር ቤቱ የውጪ ጉዳዮች ኮሚቴ አዲስ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ግሪጎሪ ሚክ በኢትዮጵያ፣ ትግራይ ክልል በተከሰተው ግጭት ዙሪያ ያለው ከፍተኛ የመረጃ እጥረት በአስቸኳይ መፈታት እንዳለበት ያሳሰቡት በዚህ ሳምንት መጀመሪያ በዓለም አቀፍ ስልት ጥናት ማዕከል አማካኝነት በተካሄደ ውይይት ላይ ነው። ሚክ በተለይ ምርጫ በደረሰበት ወቅት በክልሉ ያለውን ሁኔታ በትክክል ማወቅ በጣም አስፈላጊ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

"ገለልተኛና ነፃ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስፈልገው ሁኔታ መሟላቱ ሳይረጋገጥ ምርጫ ማድረግ አይቻልም። ስለዚህ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን የተጀመረውን ለውጥ ወደነበረበት መመለስ ነው።"

ኢትዮጵያ ስድስተኛውን አገራዊና ክልላዊ አጠቃላይ ምርጫ በግንቦት 28፣ 2013 ዓ.ም. እንደምታካሂድ ማስታወቋን ተከትሎም ሚክ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ግጭቶች ቆመው ለምርጫ አመቺ ሁኔታ የሚፈጠርበት ሁኔታ ላይ ቅድሚያ ተሰጥቶ ሊሰራ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።

"ህብረተሰቡ በሚደረገው ምርጫ እንዲተማመን፣ ሁሉም ሰው በምርጫው ላይ ለመሳተፍ እችላለሁ የሚል ስሜት እንዲሰማው መደረግ አለበት። ሌላው ግልፅ ነገር ደግሞ የሚታየው የሰብዓዊ ጉዳትና የመብት ጥሰት እንዳይቀጥል መደረግ አለበት።"

ከምርጫው ጋር ተያይዘው የሚነሱ የፀጥታና አለመረጋጋት ጉዳዮች በምርጫ ሂደቱ ላይ እየፈጠረ ያለውን ስጋት በተመለከተ ያናገርናቸው የምርጫ ቦርድ ኮምዩኒኬሽን አማካሪ ሶሊያና ሽመልስ በበኩላቸው ሀገሪቱ ያለችበት የፀጥታ ሁኔታ ከምርጫ ጋር እንደሚገኛኝ በመግለፅ በመጪዎቹ ሶስት ወራት የሀገሪቱ የፀጥታ ሁኔታ በሚሻሻልበት ሁኔታ ላይ ቦርዱ ከሚመለታቸው አካላት ጋር አብሮ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የፀጥታ ሁኔታን አስቀድሞ ማረጋገጥ ግን የቦርዱ ሀላፊነት አለመሆኑንና የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት በዚህ ጉዳይ መጠየቅ እንዳለባቸው አበክረው የገለፁት ሶሊያና የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ባሉበት ሆነው መምረጥ በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ቦርዱ እየሰራ እንደሆነም አክለው ገልፀዋል ።

የዓለም አቀፍ ስልት ጥናት ማዕከል ባዘጋጀው የድህረገፅ ውይይት ላይ ተገኝተው ውይይት ያካሄዱት ሚክ ዲሞክራቶች የተቆጣጠሯቸው የህግ አውጪውና የመወሰኛው ምክርቤቶች በአፍሪካ ላይ የሚያራምዱት አቋም ምን እንደሚመስል አብራርተዋል። ከሰሞኑ ግጭቶች የበዙባት ኢትዮጵያን ወክላ የአዲስ ስታንዳርድ ሚዲያ መስራችና ባለቤት የሆነችው ፀዳለ ለማ ወቅታዊ ጉዳዮችን ለሊቀመንበሩ አስረድታለች።

በትግራይ ክልል እየተዳሄደ ያለው ግጭት ሙሉ ለሙሉ ቆሞ ወደ ክልሉ በቂ ርዳታ እንዲዳረስ ለማድረግ ዩናይትድ ስቴትስ ከፍተኛ ግፊት ማድረግ አለባት ያለችው ፀዳለ ከምርጫው በፊት የታሰሩ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላት እንዲፈቱም ጠይቃለች።

"እያወራን ያለውነው በጣም ጥቂት የፖለቲካ ፓርቲዎች ብቻ የምርጫ ዘመቻ እያደረጉበት ስላለውና በሺዎች የሚቆጠሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና የበላይ አመራሮች የታሰሩበት ምርጫ ነው። ይህ ደግሞ በተለይ በኦሮሚያ ክልል በስፋት ይታያል።"

ከኢትዮጵያ በተጨማሪ በቅርቡ ከፍተኛ አለመረጋጋት የተከሰተበት ምርጫ ያካሄደችውን ዩጋንዳን ወክላ ጋዜጠኛና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሆነችው ሮዝቤል ኳጓሚሬ ባደረገችው ንግግርም ላለፉት 35 አመታት በስልጣን ላይ የቆዩት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር እንዲያካሂዱ አሜሪካ ግፊት እንድታደርግ ጠይቃለች።

"ብዙ ሰዎች ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ማየት ይፈልጋሉ። ያ እንዳይሆን እያደረጉ ያሉት ደግሞ 35 አመት ስልጣን ላይ የቆዩት ፕሬዝዳንት ሙሴቨኒ ናቸው። ስለዚህ ከሀገሪቱ ጋር የሚኖራችሁ ግንኙነት ሀገራችሁ ወዴት ነው እየሄደች ያለችሁ ህዝቡ የተለመደ ስነስርዓት ሳይሆን ትክክለኛ ምርጫ ይፈልጋል በሚል ጠንካራ ንግግር ላይ የተመሰረተ መሆን አለበት።"

አዲሱ የባይደን አስተዳደር፣ ኢትዮጵያንና ዩጋንዳን ጨምሮ፣ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር በሚኖረው ግንኙነት ዋና ትኩረቱን የሚያደገው ድምበር ተሻጋሪ በሆኑ ችግሮች ዙሪያ መሆኑን ሚክ በውይይቱ ወቅት አበክረው ተናግረዋል።

በትራምፕ አስተዳደር ወቅት አፍሪካ እኩል ድምፅ እንዳይኖራት የበታች ተደርጋ ቆይታለች ያሉት ሚክ የአየር ንብረት፣ ኢኮኖሚ፣ ሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች የባይደን አስተዳደር በአፍሪካ ዙሪያ የሚያተኩርባቸው ጉዳዮች እንደሆኑ አስረድተዋል። በተለይ ሰላምና ፀጥታን በተመለከተ በአህጉሪቱ ውስጥ ተቀማጭ የሆኑ የዩናይትድ ስቴትስ ወታደሮች ሚናና አስፈላጊነት እንደገና እንደሚፈተሽ የጠቆሙት ሚክ ዩናይትድ ስቴትስ በሚቀጥሉት አስር አመታት አለመረጋጋት የሰፈነባቸው ሀገራትን ቁጥረ በግማሽ ለማውረድ አልማ እንደምትሰራ ተናግረዋል።

XS
SM
MD
LG