በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ብሪታኒያ ጁሊያን አሳንጌን ለአሜሪካ አሳልፋ እንደማትሰጥ አስታወቀች


ብሪታኒያ ጁሊያን አሳንጌን ለአሜሪካ አሳልፋ እንደማትሰጥ አስታወቀች
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:36 0:00

የተደበቁና ህገወጥ የሆኑ ሚስጥሮችን ለህዝብ ይፋ በማድረግ የሚታወቀው የዊኪሊክስ ድህረገፅ መስራች ጁሊያን አሳንጌ፣ ለቀረበበት የኮምፒውተር ሰርጎ ገብነትና ሚስጥራዊ መረጃዎችን ስርቆት ክስ ምላሽ እንዲሰጥ በሚል ዩናይትድ ስቴትስ ተላልፎ እንዲሰጣት የጠየቀችውን ጥያቄ የብሪታኒያ ዳኛ ውድቅ አድርገውታል። ዳኛው ተላልፎ የመሰጠቱን ጥያቄ ውድቅ ያደረጉት አሳንጌ በአሜሪካ እስር ቤት ውስጥ እራሱን ሊያጠፋ ይችላል በማለት ነው።

ለንደን የሚገኘው ፍርድቤት ዳኛ ጁሊያን አሳንጌ ለዩናይትድ ስቴትስ ተላልፎ እንደማይሰጥ ውሳኔ ሲያሳልፉ የአሳንጌ ደጋፊዎች ከፍርድ ቤቱ ውጪ ተሰብስበው ደስታቸውን ገልፀዋል። ከነዚህ አንዷ የአሳንጌ ጉዋደኛ የሆነችው ስቴላ ሞሪስ ናት።

"የዛሬው ደስታ በዚህ ጉዳይ ወደ ፍትህ አንድ ርምጃ የሚወስድ ነው።"

የብሪታንያ ዳኛ ውሳኔያቸውን ሲያሳልፉ አሳንጌ አሜሪካን አገር በቨርጂንያ ክፍለ ግዛት፣ አሌክሳንድሪያ በሚገኘው ፍርድቤት ተገቢውን የፍርድ ሂደት እንደሚያገኝ እንደሚያምኑ፣ የቀረበበትንም ክስ ቀርቦ ምላሽ መስጠት እንዳለበት ገልፀዋል። ሆኖም አሉ ዳኛዋ፣ አሳንጌ በከፍተኛ ጭንቀት የሚሰቃይ በመሆኑ፣ አሁን ባለበት ሁኔታ ለብቻው ተዘግቶበት እስር ቤት ውስጥ ቢገባ የአሜሪካ እስር ቤት ስርዓ እራሱን ከማጥፋት ሊያድነው አይችልም።

የአሳንጌ ጠበቃ የሆነቸው ጄኔፈር ሮቢንሰን ዳኛዋ ያሳለፈቱን ይህን ውሳኔ በተመለከተ እንዲህ ትላለች።

"ይሄ በጣም እንፈልገው የነበረው ውሳኔ እና ልናከብረው የሚገባ አሸናፊነት ነው። ነገር ግን በዛው ልክ ደግሞ በመናገር ነፃነት ዙሪያ ባለው የክሱ አካል ላይ ዳኛዋ በጣም አስቸጋሪ የሆነ ውሳኔ እንዳሳለፉ መርሳት የለብንም።"

የአሳንጌ ጠበቃዎች ክሱ የፖለቲካ እንደሆነና አሳንጌን አሳልፎ መስጠት ጋዜጠኝነትን አደጋ ላይ ይጥለዋል ሲሉ የሚያቀርቡትን የክርክር ሀሳብ አሜሪካ አትቀበለውም። የፕሬስ ነፃነት ተሟጋቾች ግን የፍድቤቱን ውሳኔ በደስታ ተቀብለውታል።

እ.አ.አ. በ 2010 እና 2011፣ አሳንጌ ዊኪሊክስ በተሰኘው ድህረገፁ ከኢራቅና አፍጋኒስታን ጋር የተያያዙ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዲፕሎማሲያዊ የመረጃ ልውውጦችና ወታደራዊ ሪፖርቶች ታትመው እንዲወጡ አድርጓል። አሳንጌ ያወጣቸው መረጃዎች፣ የአሜሪካ ወታደሮች በንፁህ የኢራቅ ሲቪሊያንን ላይ የፈፀሙትን ግድያ የሚያሳዩ ቪዲዮዎችን ጨምሮ ሌሎች ተገቢ ያልሆኑ አድራጎቶቻቸውን ያጋለጠ እንደሆነ ተናግሯል።

አሜሪካ በበኩሏ አሳንጌ ሚስጥራዊ የሆኑ ሰነዶችን ሰርቆ በማውጣት የሀገርን ደህንነት አደጋ ላይ ጥሏል፣ ለአሜሪካ መረጃ ያቀብሉ የነበሩ ሰዎችን ማንነት በመግለፅም ህይወታቸው አደጋ ላይ እንዲወድቅ አድርጓል ስትል በውንጀል ከሳዋለች። የብሪታኒያው ዳኛ ግን በአሳንጌ ደህንነት ዙሪያ ያለው ስጋት ከአሜሪካ ክስ የበለጠ ያመዝናል ሲሉ ፍርዳቸውን ሰጥተዋል።

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት፣ በዩናይትድ ስቴትስ ብሔራዊ ፀጥታ ጉዳይና የህዝብ ነፃነት ዙሪያ በመፃፍ የሚታወቁት አሜሪካዊቷ ሜርሲ ዊለር፣ እንዲህ ብለዋል፣

"አሜሪካ ከብሪታኒያ ሰዎች ተላልፈው እንዲሰጧት በምትሞክራቸው ሙከራዎች ይሄ ሲፈጠር ለሶስተኛ ጊዜ ነው። በሽብር ክስ የተከሰሱ ሰዎች ላይም በተመሳሳይ ትንቅንቅ የተደረገባቸው ክርክሮችም ነበሩ።"

ዊለር ጨምረው፣ ዩናይትድ ስቴትስ በፍርዱ ላይ ይግባኝ ብትጠይቅም፣ አሳንጌ የቀረበበትን ክስ ከብሪታኒያ ሆኖ ሊከታተል የሚችልበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል ይላሉ።

"አሜሪካ እና ብሪታኒያ በዚህ መልኩ ትብብር ሊያደርጉ ይችላሉ ብዬ አስባለሁ ምክንያቱም ይሄ የብሔራዊ ፀጥታ ጉዳይን በተመለከተ የሚያደርጉት አይነት ጉዳይ ነው። በአሜሪካ የቀረበው ክስ በስምምነት ለአሜሪካ መረጃ ያቀብሉ የነበሩ ሰዎችን ማንነት እንዳጋለጠ ይጠቅሳል ግን ለአሜሪካ ብቻ ሳይሆን ለብሪታኒያም መረጃ ያቀብሉ የነበሩ ሰዎችን ሊጨምር እንደሚችልም ታሳቢ ሊደረግ ይገባል።"

አሳንጌ ከዩናይትድ ስቴትስ ሸሽቶ በሄደበት ስዊድን በአስገድዶ መድፈር በመጠርጠሩ እ.አ.አ በ 2012 ለንደን በሚገነው የኢኩዋዶር ኤምባሲ ጥገኝነት ጠይቆ ለሰባት አመት ቆይቷል። ሆኖም በ2019 ሚያዚያ ወር ላይ ኢኩዋዶር የብሪታኒያ ፖሊሶች እንዲወስዱት በመፍቀዷ ለ50 ሳምንታት በእስር ቆይቷል።

አሁንም በለንደን እስር ቤት የሚገኘው አሳንጌ በጠበቆቹ አማካኝነት ላቀረበው የዋስትና ጥያቄ ምላሽ ለማግኘት እየተጠባበቀ ይገኛል። ተላልፎ ለመሰጠቱ ጉዳይ የቀረበው የይግባኝ ጥያቄ ሂደትም በርካታ ወራትን ሊፈጅ እንደሚችል ተጠቁሟል።
XS
SM
MD
LG