በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ ገና ብዙ መስራት ይጠይቃል


የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ ገና ብዙ መስራት ይጠይቃል
please wait

No media source currently available

0:00 0:08:35 0:00

ከኢትዮጵያ በጉዲፈቻ ወደ ተለያዩ ሀገራት ይወሰዱ የነበሩ ህፃናት በሚደርስባቸው የማንነት ቀውስና በአሳዳጊዎቻቸው በሚደርስባቸው በደል ምክንያት የውጪ ጉዲፈቻ ሙሉ ለሙሉ ከታገደ ሶስት አመታትን አስቆጥሯል። በዚህም ምክንያት የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ እያደገ መሆኑን የአዲስ አበባ ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ቢያስታውቅም በዘርፉ የሚሰሩ በጎ አድራጎት ድርጅቶች ግን እድገቱ ጅማሮ እንጂ በቂ አይደለም ይላሉ።

ኢትዮጵያውያን ለጉዲፈቻ እንግዳ አይለሉም። በተለያዩ ባህላዊ ሀይማኖታዊና ህጋዊ ስነ ስርዓቶች ወላጅ አልባ ወይም ረጂ የሌላቸውን ህፃናት በጉዲፈቻ ወስዶ ማሳደግ የሀገሪቱ ባህል መገለጫ ሆኖ ኖሯል። ነገር ግን በተለያዩ ጊዜያት ያጋጠሙ እንደ ረሀብ የመሳሰሉ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ አደጋዎች የህብረተሰቡን አቅም በማዳከማቸው የሀገርው ውስጥ የጉዲፈቻ ባህልም አብሮ ተቀዛቀዘ። በአንድ ወቅት የብዙ ተቋማትና ግለሰቦች የገንዘብ ምንጭ የነበረው የውጪ ጉፈቻ በፍጥነት ማደግም የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻውን ጭራሽ አጠፋው። ከ1992 ዓ.ም. አንስቶ የውጪ ጉዲፈቻ እስከታገደበት 2009 ዓ.ምህረትም ከ 40 ሺህ ኢትዮጵያውያን ህፃናት በላይ በጉዲፈቻ ወደ ውጪ ሀገራት ተወስደዋል። በአሜሪካ ብቻም ከ 16 ሺህ በላይ ኢትዮጵያዊ ህፃናት እንዳሉ መረጃዎች ያሳያሉ።

በኢትዮጵያ ጉዲፈቻ ዙሪያ ለበርካታ አመታት የሰራውና ሴንተር ፎር ፋሚሊ (የቤተሰብ አገልግሎት ማዕከል) የተሰኘው በጎ አድራጎት ድርጅት መስራችና ስራ አስኪያጅ የሆነው አቶ ተፈራ ሀይሉ በጉዲፈቻ ወደ ውጪ የሚወሰዱ ህፃናት የሚያጋጥሟቸው የነበሩ ችግሮችን እንዲህ ይገልፀዋል።

እነዚህን ጉዳቶች መሰረት አድርጎ መንግስት ከ 2009 ዓ.ም. ጀምሮ የውጪ ጉዲፈቻ እንዲታገድ አድርጓል። የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት /UNICEF/ የቅርብ መረጃ እንደሚያሳየው ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ከ 4.5 ሚሊዮን በላይ ወላጅ አልባ ህፃናት ይገኛሉ። አቶ ተፈራም መንግስት የወሰደው ድንገተኛ እርምጃ እነዚህን ህፃናት ያላገናዘበ ነበር ይላል።

ቁጥሩ እንደሚያሳየው የውጪ ጉዲፈቻ ከታገደ በኃላ የሀገር ውስጥ ማደጎው በተወሰነ ደረጃ ጭማሪ አሳይቷል። ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ አስቸኳይ ርዳታ ከሚፈልጉ ወላጅ አልባና በኢኮኖሚ ችግር ውስጥ የሚኖሩ ህፃናት ቁጥር አንፃር በአሁኑ ሰዓት ብቸኛ አማራጭ የሆነው የሀገር ውስጥ ማደጎ ዙሪያ ገና ብዙ ሊሰራ እንደሚገባ አቶ ተፈራ ያስረዳል።


የሀገር ውስጥ የማደጎ ሂደት ከመፈለግ ይጀምራል ይላል አቶ ተፈራ። የሴቶችና ህፃናት ቢሮ ባስቀመጠው መስፈርት መሰረትም ህፃናትን በማደጎ መውሰድ የሚፈልጉ ሰዎች ኢትዮጵያዊ መሆናቸውን የሚያሳይ መታወቂያ፣ በቂ ገቢ እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ፣ የህክምና ማረጋገጫ፣ የጋብቻ ማስረጃ እና የድጋፍ ደብዳቤ የመሳሰሉ አስር መስፈርቶችን ማሟላት ይኖርባቸዋል። ሴንተር ፎር ፋሚሊ የተሰኘው የተፈራ ድርጅትም ህብረተሰቡን ስለጉዲፈቻ ከማስተማር አንስቶ ኢትዮጵያዊ ጉዲፈቻ አድራጊዎች አስፈላጊውን መስፈርት አሟልተው እንዲገኙ በማገዝ ይሰራል።

የሀገር ውስጥ ማደጎ ተፈራ በሴንተር ፎር ፋሚሊ ሰርቪስ ውስጥ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራበት ጉዳይ ነው። ህብረተሰቡ በጉዲፈቻ ዙሪያ ያለውን እውቀት ከማጎልበት አንስቶም እስከ የድህረ ማደጎ አገልግሎቶች ድረስ ለመስራትም ከሴቶችና ህፃናት ሚኒስቴር አብሮ በመስራት ላይ እንደሚገኝ ተፈራ ይገልፃል።
XS
SM
MD
LG