በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በኮቪድ 19 ዙሪያ ለሚሰሩ የጤና ዘርፍ ሰራተኞች የተፈቀደው አበል እስካሁን አልተከፈለም


Ethiopiaon doctors attend training to use mechanical ventilators for COVID-19 patients at the American Medical Center (AMC) in Addis Ababa, Ethiopia, on April 1, 2020. (Photo by Michael Tewelde / AFP)
Ethiopiaon doctors attend training to use mechanical ventilators for COVID-19 patients at the American Medical Center (AMC) in Addis Ababa, Ethiopia, on April 1, 2020. (Photo by Michael Tewelde / AFP)

የኮቪድ 19 ወረርሽኝን በመከላከልና የህክምና አገልግሎት በመስጠት በቀጥታ ለሚሳተፉ የጤና ዘርፍ ሰራተኞች የተጋላጭነት ልዩ አበል እንዲከፈላቸው የሚያዘው አዋጅ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ፀድቆ ከወጣ ስድስት ወር ቢያልፈውም እስካሁን ክፍያው አልተፈፀመም። ደሞዝም ግዜውን ጠብቆ ስለማይከፈል በኮቪድ 19 ዙሪያ የሚሰሩ ባለሙያዎች ለኢኮኖሚ ጫና መዳረጋቸውንም ተናግረዋል።

በኮቪድ 19 ዙሪያ ለሚሰሩ የጤና ዘርፍ ሰራተኞች የተፈቀደው አበል እስካሁን አልተከፈለም
please wait

No media source currently available

0:00 0:08:51 0:00


የጤና ዘርፍ ሰራተኞች የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ለመቆጣጠርና ለማከም በሚደረገው ጥረት ለበሽታው ያላቸውን ከፍተኛ ተጋላጭነትና እያበረከቱት ያለውን አስተዋፅኦ ከግምት ውስጥ በማስገባት የሚኒስትሮች ምክር ቤት ልዩ አበል እንዲከፈላቸው ውሳኔ ያስተላለፈው ግንቦት 14፣ 2012 ዓ.ም. ነበር።

ነገር ግን ይህ ውሳኔ እስካሁን ተፈፃሚ እንዳልሆነና ወረርሽኙን ለመቆጣጠር በቀጥታ ተሳታፊ ሆነው የሚሰሩ የጤና ባለሙያዎችም ሆኑ ድጋፍ ሰጪ አካላት ምንም አይነት የአበል ክፍያ እያገኙ እንዳልሆነ በተለያዩ ክልሎች ያነጋገርናቸው የጤና ባለሙያዎች ይገልፃሉ።

ከነዚህ ውስጥ በደቡብ ክልል፣ ወላይታ ዩንቨርስቲ ውስጥ በሚገኝ የኮሮና ህክምና ማዕከል ውስጥ፣ ላለፉት አምስት ወራት ከቤተሰብ ተነጥላ የኮሮና ቫይረስ ህሙማንን እያከመች የምትገኘው ዶክተር አዲስ ሀብታሙ አንዷ ናት።

በተመሳሳይ ካለፈው አመት ሚያዚያ ወር ጀምሮ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን የኮኖና ለይቶ ማቆያና ህክምና ማዕከል ውስጥ በማገልገል ላይ የሚገኙት ዶክተር ኤፍሬም ቸርነት፣ ምልክት ከማያሳዩ ህመምተኞች አንስቶ በመተንፈሻ መርጃ መሳሪያ እርዳታ እስከሚታከሙ ህመምተኞች ድጋፍ የሚያደርጉ የጤና ባለሙያዎች ለወረርሽኙ ያላቸውን ተጋላጭነት ገልፀው፣ ይህ ታሳቢ ተደርጎ እንዲከፈላቸው የተፈቀደው የአበል ክፍያ ባለመፈፀሙ እንዳሳዘናቸው ያስረዳሉ።

በሚንስትሮች ምክርቤት እንዲከፈል ታዞ የነበረው ልዩ አበል እስካሁን ካለመከፈሉ በተጨማሪ፣ የህክምና ባለሙያዎቹ የሚከፈላቸው ደሞዝ ለኑሮ በቂ አለመሆኑና ጊዜውን ጠብቆ አለመሰጠቱም የህክምና ባለሙያዎቹንና በድጋፍ ሰጪናነት የሚያገለግሉ አካላትን የኢኮኖሚ ችግር ውስጥ እንደከተታቸው ዶክተር ኤፍሬም ጨምረው ያስረዳሉ።

በሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ መሰረት በኮቪድ 19 ወረርሽኝ ዙሪያ የሚሳተፉና ልዩ የአበል ክፍያ እንዲከልፈላቸው የተወሰነው ወረርሽኑን ለመከላከል ለተቋቋመው ግብረ ኃይል አስተባባሪዎች፣ ሀኪሞች፣ አምቡላንስ ላይ የሚሰሩ ሰራተኞች፣ የፅዳት፣ የጥበቃና የምሰሳሰሉት ስራዎችን የሚሰሩ ድጋፍ ሰጪ አካላት ሲሆን የክፍያው መጠንም እንደየስራ ድርሻቸው በቀን ከ1150 እስከ 300 ብር እንዲሆን ያዛል።

ዶክተር ኤፍሬም ይህ ክፍያ አዲስ አበባ ከተማ በኮቪድ 19 ዙሪያ ለሚሰሩ ሀኪሞች ሁለት ግዜ መከፈሉን ገልፀው፣ በሌሎች ክልሎች ላይ ለሚገኙ ሀኪሞች አለመከፈሉ ግን የበለጠ ጥያቄ ፈጥሮብኛል ይላሉ።

ሌላው በጉዳዩ ላይ ያነጋገርነው ዶክተር እሸቱ ታደሰ በቦንጋ ከተማ በሚገኘውና በከፋ ዞን ውስጥ ብቸኛ በሆነው የኮኖና ህክምና ማዕከል ውስጥ የአካባቢ ጤና አጠባበቅ ባለሙያና የ4ኛ አመት የህክምና ተማሪ ነው። ከማዕከሉ በተጨማሪ ለኮሮና ታማሚዎች የቤት ለቤት የህክምንና አገልግሎት የሚሰጠውና ነፍሳችንን ገብረን ነው የምናገለግለው የሚለው ዶክተር እሸቱ የሚከፈላቸው ደሞዝ ለቤት ኪራይ፣ ለምግብ እና ለመሳሰሉት መሰረታዊ ወጪዎች እንኳን እንደማይበቃ በመግለፅ የህክምና ባለሙያው ያለበትን ቅሬታ እንዲህ ያስረዳል።

ዶክተር እሸቱ ጨምሮ፣ በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች መካከል ያለው የአበል አከፋፈል ልዩነትና የደሞዝ መዘግየት እንዲስተካከልም ጠይቋል።

የህክምና ባለሙያዎቹ የአበል ክፍያ ጥያቄያቸውን ለሚገኙባቸው ዞኖችና ክልሎች አቅርበው በቂ መልስ ባለማግኘታቸው ጤና ሚኒስቴርን ጨምሮ ወደ ሌሎች የሚመለከታቸው የፌደራል መስሪያ ቤቶች ቅሬታቸውን ለማዝገባት እየተዘጋጁ መሆኑን ነግረውናል። በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡን የጤና ሚኒስቴርን ለማግኘት በተደጋጋሚ ያደረግነው ጥረት ለጊዜው ባይሳካም፣ ምላሻቸውን ካገኘን ጉዳዩን ይዘን እንመለሳለን።

XS
SM
MD
LG