አሜሪካ ቪየትናም የዩክሬንን ሉዓላዊነት እንድትደግፍ አሳሰበች

  • ቪኦኤ ዜና

የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን እና የቪየትናም ፕሬዚዳንት ቶ ላም በቬትናም ዋና ከተማ ሃኖይ

የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በሃኖይ ያደረጉትን የአንድ ቀን ጉብኝት ተከትሎ ቪየትናም የዩክሬንን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት እንድትደግፍ ዩናይትድ ስቴትስ አሳሰበች።

ፑቲን ወደ ቪየትናም የተጓዙት በሰሜን ኮሪያ የነበራቸውን የሁለት ቀናት ቆይታ ተከትሎ ሲሆን፣ እየተባባሰ የመጣውን የምዕራባውያን ማዕቀም ለመጋፈጥ የሚያስችላቸው ጥምረት ለመፍጠር በእስያ የሚያደርጉት ጉብኝት አካል ነው።

የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማቲው ሚለር ትላንት ኀሙስ ዕለታዊ መግለጫቸውን በሰጡበት ወቅት ለቪኦኤ በሰጡት ምላሽ "ማንኛውም ሀገር ከሩሲያ መንግሥት ጋራ ሲወያይ እና በተለይም ከሩሲያ መንግሥት የተውጣጡ መሪዎችን ሲያስተናግድ፣ ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነትን ጨምሮ ለተባበሩት መንግስታት ቻርተር መርሆዎች ያላቸውን አክብሮት በግልፅ ያሳያሉ ብለን እንጠብቃለን። እነዚያ መርሆዎች በዓለም ዙሪያ መከበር አለባቸው” ብለዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ አሜሪካ እና ቪየትናም ባለፈው ዓመት የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ካሻሻሉ በኋላ በዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የእስያ ከፍተኛ ዲፕሎማት ወደ ሃኖይ እየተጓዙ መሆኑ ተመልክቷል።

የምስራቅ እስያ እና የፓስፊክ ጉዳዮች የውጭ ጉዳይ ረዳት ፀሃፊ የዳንኤል ጄ. ክሪተንብሪንክ ጉዞ ፑቲን ሃኖይን ከመጎበኘታቸው በፊት አስቀድሞ ታቅዶ እንደነበር ቃል አቀባዩ ሚለር ተናግረዋል።

የቪየትናም ኩባንያዎች ወይም ግለሰቦች ሞስኮ ዩክሬን ላይ ለምታካሂደው ጦርነት የቁሳቁስ ድጋፍ እየሰጡ እንደሆነ ወይም ዋሽንግተን ሃኖይን በዚህ ጉዳይ አስጠንቅቃ እንደሆነ፣ በሚል ሚለር ከዘጋቢዎች ለቀረበላቸው ምንም ግምገማ አልነበራቸውም፡፡