ኢትዮጵያንና ሶማሊያን ለማሸማገል ጥረቷን እንደምትቀጥል ቱርክ አስታወቀች

የቱርክ የውጪ ጉዳይ ምኒስትር ሃካን ፊዳን

ኢትዮጵያንና ሶማሊያን ለማሸማገል ጥረቷን እንደምትቀጥል ቱርክ ትላንት ሐሙስ አስታወቀች፡፡

የቱርክ የውጪ ጉዳይ ምኒስትር ሃካን ፊዳን ከኢትዮጵያው አቻቸው ታዬ አጽቀ ሥላሴ እና ከሶማሊያው የውጪ ጉዳይ ምኒስትር አህመድ ሞአሊም ፊቂ ጋራ ኒው ዮርክ ውስጥ መገናኘታቸው ታውቋል።

ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋራ የተፈራረመችውን የመግባቢያ ሰነድ ተከትሎ፣ ከሶማሊያ ጋራ ለገባችበት ንትርክ መፍትሄ ለመሻት ቱርክ አንካራ ላይ በሁለቱ ወገኖች መካከል ሁለት ቀጥተኛ ያልሆነ ንግግር ማስተናገዷ ይታወሳል።

SEE ALSO: ሶማሊያ ለኢትዮጵያ ነቀፌታ ምላሽ ሰጠች

ከፊዳን ጋራ የነበራቸው ውይይት ገንቢ እንደነበር ፊቂ በ X ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ አስታውቀዋል።

አሁን የሚስተዋለውን ውጥረት ለማርገብ፣ ሁለቱንም ወገኖች ተጠቃሚ ያሚያደርግ ተመጣጣኝ እንዲሁም መተግበር የሚችል መፍትሄ የሚያመጣ ሥራ ለመሥራት መወሰናቸውን የቱርኩ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በX ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በለጠፈው መልዕክት አስታውቋል።

የሁለቱ ወገኖች አቋም ተመሳሳይ ሲሆን፣ የቱርክ ባላሥልጣናት በተናጥል እንደሚያነጋግሯቸው ሃካን ፊዳን ማስታወቃቸውን የሮይተርስ ዘገባ አመልክቷል።

SEE ALSO: ኢትዮጵያ ግብጽ በሳምንቱ መጨረሻ ወደሶማሊያ በድጋሚ የጦር መሣሪያዎች መላኳን በሚመለከት ያላትን ሥጋት ገለጸች

ታዬ አጽቀ ስላሴ ትላንት ከአሜሪካው የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ፀሃፊ ካትሪን ሞሊ ፊ ጋራ በተገናኙበት ወቅት፣ ኢትዮጵያ በሶማሊያ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የምታደርገውን ጥረት እነድምትቀጥልና አሁን ያለውን የአፍሪካ የሽግግር ልዑክ በአዲስ ኃይል ለመተካት ከመወሰኑ በፊት ጥንቃቄ እንዲደረግና ሁሉም ጉዳዮች ከግምት እንዲገቡ ጠይቀዋል።