ኮሌራ ማላዊ ውስጥ 1200 ሰው ገደለ

  • ቪኦኤ ዜና

ማላዊ በታሪኳ ከምንጊዜውም የከፋ የኮሌራ ወረርሽኝ ላይ እንደምትገኝ የዓለም የጤና ድርጅት ባለሥልጣናት ገለጹ።

ማላዊ በታሪኳ ከምንጊዜውም የከፋ የኮሌራ ወረርሽኝ ላይ እንደምትገኝ የዓለም የጤና ድርጅት ባለሥልጣናት ገለጹ። በሀገሪቱ ኮሌራ ከ1200 በላይ ሰዎች የገደለ ሲሆን ካለፈው መጋቢት ወዲህ 37 ሺህ ሰዎች መታመማቸውን የዓለም የጤና ድርጅት ባለሥልጣናት አመልክተዋል።

የማላዊ መንግሥት የኮሌራ ወረርሽኙን አጣዳፊ የጤና አደጋ ብሎ ባለፈው ታህሳስ አውጇል። የዓለም የጤና ድርጅት የአገር አቀፍ ምላሽ ዕቅድ ማዘጋጀትን ጨምሮ የተለያዩ ዕርምጃዎች መውሰዱን አስታውቋል።

የመንግሥታቱ ድርጅት ማላዊ ውስጥ ሁለት ግዙፍ የኮሌራ ክትባት ዘመቻዎች ማካሄዱ የተገለጸ ሲሆን በክትባት አቅርቦት ዕጥረት የተነሳ ሁለት ክትባት መሰጠት ሲኖርበት የተቻለው አንድ ክትባት ብቻ መሆኑን ገልጿል።

የዓለም የጤና ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም እንዳሉት ባሁኑ ወቅት የኮሌራ ወረርሽኝ ያለባቸው ሀገሮች ቁጥር 23 መድረሱን አመልክተዋል።