ሰሜን ኮሪያ አዲስ ተወንጫፊ ሚሳይል ለሙከራ ተኩሰች

  • ቪኦኤ ዜና
ሰሜን ኮሪያ አዲስ አህጉር ተሻግሮ ተወንጫፊ ሚሳይል ለሙከራ ተኩሳለች።

ፒዮንግያንግ ካለፈው መስከረም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ የተኮሰችው ሚሳይል ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ማናቸውም ስፍራ ሊደርስ የሚችል ነው ስትል ማወጁዋ ውጥረቱን አባብሶታል።

ዛሬ ረቡዕ የሰሜን ኮሪያ መንግሥት ቴሌቭዥን ባስተላልፈው ዜና

አዲሱ አህጉር ተሻጋሪ ሚሳይል “ህዋሶንግ 15” የኮሪያ ሠራተኞች ፓርቲ ባደረገው ስትራተጂያዊና ፖለቲካዊ ውሳኔ መሰረት ሙከራው በስኬት ተከናውኗል ብሉዋል።

ሰሜን ኮሪያ ካሁን ቀደም ሚሳይል ለሙከራ ስትተኩስ ዩናይትድ ስቴትስ የትኛውን ቦታ ሊመታ የሚችል ነው የሚል መግለጫ ስትሰጥ የቆየች ቢሆንም ያን ለማድረግ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚያስችላት ተሽሽሎ በተሰራው በአዲሱ ሚሳይል መሆኑ ተነግሯል።

ሰሜን ኮሪያ ራሱዋ ብቻ ሳትሆን የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናትም ያቺ ሀገር ካሁን ቀደም ለሙከራ ከተኮሰቻቸው በበለጠ ከፍታ መወንጨፍ የሚችል እንደሆን ተናግረዋል።

የዩናይትድ ስቴትስ የመከላከያ ሚኒስትር ጂም ማቲስ እንደ እውነቱ ከሆነ ይሄኛው ካሁኑ ቀደም ከተኮሰቻቸው በበለጠ ከፍታ ተወንጭፏል ማለታቸው ተጠቅሷል።

ሙከራውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትረምፕም ለጋዜጠኞች በሰጡት አስተያየት “መላ ይበጅለታል” ብለዋል። መላውን በዝርዝር ባይናገሩም ሰሜን ኮሪያ ላይ ግፊቱን ከፍ ማደረግን የሚጨምረውና ሁሉንም አማራጭ ክፍት ያደረገው የዩናይትድ ስቴትስ አቋም እንዳልተቀየረ አመልክተው፣ ትልቅ ክብደት የሚሰጠው ጉዳይ ነው ማለታቸው ተጠቅሷል።

ደቡብ ኮሪያ በበኩሉዋ ፒዮንግያንግ በተኮሰች በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ የራሱዋን ሚሳይል ለሙከራ በመተኮስ ፈጣን እና ትክክለኛ በትክክል የተነጣጠረ አፀፋ ለመመለስ ብቃቱ እንዳላት ለሰሜን ኮሪያ አሳይታለች።