በኔዘርላንድ በኮቪድ ገደቦች ምክኒያት የተቀሰቀሰው ተቃውሞ

  • ቪኦኤ ዜና

በኮቪድ-19 ገደቦች ምክኒያት በኔዘርላንድ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ሦስትኛ ምሽት አስቆጥሯል።

በኮቪድ-19 ገደቦች ምክኒያት በኔዘርላንድ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ሦስትኛ ምሽት አስቆጥሯል። በኔዘርላንድ የኮቪድ -19 ወረርሽኝ ሥርጭትን ለመቀነስ መንግሥት ያስቀመጠውን የእንቅስቃሴ ጊዜ ገደብ የተቃወሙ ነዋሪዎች ያስነሱት ተቃውሞ ሦስተኛ ቀኑን ያስቆጠረ ሲሆን በአንዳንድ ቦታዎች እሳት በማቀጣጠል፣ ድንጋይ በመወርወር እና ሱቆችን በመዝረፍ ተግባር ላይ ተሰማርተዋል በሚል እስካሁን 150 ሰዎች መታሰራቸው ታውቋል።

ፖሊስ በሮተርዳም እና በአምስተርዳም ከተማ ተቃዋሚዎቹ የፈጠሩትን አመጽ ለመግታት እና ለማብረድ ፖሊስ እንባ አምጪ ጋዞችን ተጠቅመዋል። አመፁ በተመሳሳይ እንደ ሃርለም፣ ጊሊየን እና ዴን ቦሽ ወደተባሉ ከተሞችም ጭምር የተዘማተ ሲሆን እስካሁን 10 ፖሊሶች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል።

ተቃዋሚዎቹ ቅዳሜ ዕለት ተቃውሞውን ያስነሱት መንግስት ክሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ የመጀመሪያ የሆነውን ሰዓት እላፊ የኮሮና ቫይረስ ስርችትን ለመግታት ሲል በመጣሉ ምክኒያት ነው።

የኔዘርላንድ መንግሥት ሰዓት ዕላፊ የሚጨመረውን የእንቅስቃሴ ገደብ ያወጣው በቀላሉ የሚዛመተውና ብሪታኒያ ውስጥ የተከሰተውን አዲሱን አይነት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት አስመልክቶ ከብሔራዊው የጤና ተቋም ያገኘውን የቅድመ ማስጠንቀቂያ መነሻ አድርጎ መሆኑን አስታውቋል።

በሌላ በኩል ነዋሪዎቹ ላለፉት በርካታ ሳምንታት በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ማሽቆልቆሉን በመጥቀስ “እንዲህ ያለ ሰዓት እላፊ አያስፈልገንም” በሚል ምክኒያት ተቃውሞ አስነስተዋል።

“የወንጀል ጥቃት ነው የተፈፀመው” ያሉት የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ሩቴ የተቃዋሚዎቹን ድርጊት አውግዘዋል። “ያየነው ነገር በነፃነት ከመንቀሳቀስ መብት ጋር ምንም የሚያያይዘው ነገር የለም” ካሉ በኋላ።

የወሰድናቸውን እርምጃዎች የወሰድናቸው ለመዝናናት አይደለም። ነፃነታችንን የነጠቀንን ቫይረስ ለመዋጋት ነው ብለዋል። በኔዘርላንድ እስካሁን 13 ሺሕ ሰዎች በቫይረሱ ሕይወታቸው ሲያልፍ 966 ሺሕ ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ተይዘዋል።