ሄዝቦላህ 200 ሮኬቶችን በእስራኤል ላይ አዘነበ

  • ቪኦኤ ዜና

የሄዝቦላህ አዛዥ የነበሩትን መሐመድ ናአሜህ ናስር

ዘጠኝ ወር ያስቆጠረው የጋዛ ጦርነት ውጥረቱ እየተባባሰ ባለበት በዚህ ወቅት የሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ ከ200 የሚበልጡ ሮኬቶችን እና ድሮኖችን የእስራኤል ጦር በሚገኙባቸው ስፍራዎች መተኮሱን አስታወቀ።

በኢራን የሚደገፈው ታጣቂ ቡድን እንዳለው ከአንድ ቀን በፊት የተተኮሱ 100 ሮኬቶችን ተከትሎ የተፈጸመው ጥቃት የተካሄደው፣ በደቡብ ሊባኖስ ውስጥ እስራኤል በከፍተኛ የሂዝቦላህ አዛዥ ላይ ለፈፀመችው ግድያ ምላሽ ለመስጠት ነው።

እስራኤል በበኩሏ አብዛኛው ነዋሪዎች ከመኖሪያቸው እንዲወጡ በተደረገበት የሰሜን ድንበር አካባቢ በደረሰው ጥቃት የሞተ ሰው ስለመኖሩ ያስታወቀችው ነገር የለም። ሆኖም በምላሹ በደቡባዊ የሊባኖስ ክፍል ላይ ጥቃት ማካሄዷን ገልጻለች።

የጋዛ ጦርነት በጥቅምት ወር ከጀመረ ወዲህ እስራኤል እና የፍልስጤሙ ታጣቂ ቡድን ሐማስ አጋር የሆነው ሂዝቦላህ፣ በየእለቱ በሚባል ደረጃ ተኩስ የሚለዋወጡ ሲሆን ወደ ሙሉ ጦርነት እንዳያመራ ተሰግቷል።

እስራኤል ከፍተኛ የሄዝቦላህ አዛዥ የነበሩትን መሐመድ ናአሜህ ናስርን የገደለችው የሊባኖስ የባህር ጠረፍ ከተማ በሆነችው ጣይር ላይ ትላንት ረቡዕ ባካሄደችው የአየር ድብደባ ነው። እስራኤል በሰኔ ወር ባካሄደችው ሌላ ጥቃት ታሌብ አብዳላህ የተሰኙ ሌላ አዛዥም ገድላለች።

በናስር የቀብር ሥነስርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ከፍተኛ የሂዝቦላህ ባለስልጣን ሀሼም ሳፊየዲን እስራኤል "እነዚህን ጀግኖች ዒላማ ማድረግ ደቡባዊውን የሊባኖስ ክፍል ያጋልጣል" ብላ እንዳታስብ አስጠንቅቀዋል።