ኬንያ አዲስ የብድር እና የወጪ ቅነሳ እቅድ ይፋ አደረገች

  • ቪኦኤ ዜና

ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ

በኬንያ ረቂቅ የግብር ጭማሪ አዋጅን በመቃወም በተካሄዱ ሰልፎች ላይ የ39 ሰዎች ህይወት ማለፉን ተከትሎ፣ ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ አዲስ የብድር እና የወጪ ቅነሳ እቅዶችን ዛሬ አርብ ይፋ አድርገዋል።

በምስራቅ አፍሪካዊቷ ሀገር የግብር ጭማሪውን በመቃወም ለወራት የተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ፣ ፖሊስ ወደ ፓርላማ ሊገቡ በሞከሩ ሰዎች ላይ ተኩስ በመክፈቱ ወደ ሁከት ተቀይሯል።

በሃያዎቹ ዕድሜ ውስጥ ያሉ ኬንያውያን ወጣቶች የመሩት ሰላማዊ ሰልፍ በአመታዊ የፋይናንስ ረቂቅ አዋጅ ላይ ቁጣቸውን የገለፁበት ሲሆን፣ ሀገሪቱ ከፍተኛ የገንዘብ እጥረት እንዳለባት ያስጠነቀቁት ሩቶ ረቂቅ አዋጁን እንዲያነሱ አስገድዷቸዋል።

ሩቶ ዛሬ በሰጡት መግለጫ "ጠቅላላው 346 ቢሊየን ዶላር ሳይሆን የ177 ቢሊዮን ዶላር በጀት እንዲቀነስ ለብሔራዊ ምክር ቤቱ እናቀርባለን" ብለዋል።

ኬንያ ያለባት ብድር 78 ቢሊየን ዶላር የሚደርስ ሲሆን፣ ከአጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርቷ 70 ከመቶውን ይሸፍናል።

ሩቶ አክለው የብድር ውሳኔው መንግሥት ያለበትን የበጀት ጉድለት "ከ3.3 በመቶ ወደ 4.6 በመቶ" ከፍ ቢያደርገውም ለአንዳንድ አገልግሎቶች ክፍያ እንደሚውል ተናግረዋል። እነዚህ ክፍያዎች የሁለተኛ ድረጃ መምህራንን እና ተለማማጅ ሐኪሞችን ለመቅጠር እንዲሁም የወተት ዋጋ ለማረጋጋት እና ለአርሶ አደሮች ከለላ የሚሰጠውን የማዳበሪያ መርሃ ግብር ለመደገፍ እንደሚውልም አስረድተዋል።

የቀዳማዊት እመቤቷ እና የምክትል ፕሬዝዳንቱ ባለቤት ፅህፈት ቤቶችም የሚዘጉ ሲሆን፣ የመንግሥት አማካሪዎች ቁጥርም በግማሽ ይቀንሳል።

በተጨማሪም፣ የምክትል ፕሬዝዳንቱ ቢሮ ለመጋረጃዎች ወደ 10 ሚሊየን የሚጠጋ ሽልንግ ማውጣቱ በዚህ አመት ከተገለፀ ወዲህ አሳሳቢ ሆኖ የነበረው፣ መንግሥት ለእድሳት የመደበው በጀትም በግማሽ እንደሚቀንስ ሩቶ አስታውቀዋል።

ሩቶ አክለው "በባለስልጣናት የሚደረጉ አስፈላጊ ያልሆኑ ሁሉም ጉዞዎች ታግደዋል" ሲሉ ገልጸዋል።