​ሩቶ የታክስ ጭማሪውን ሃሳብ ቢሰርዙም በኬንያ ተቃውሞው ቀጥሏል

የኬንያ ፕሬዝደንት ዊሊያም ሩቶ መግለጫ መሰጡበት ወቅት እአአ ሰኔ 26/2024

በኬንያ ሞት ያስከተለ ተቃውሞ የጫረውን የታክስ ጭማሪ ረቂቅ ሕግ እንደማያጸድቁ የሃገሪቱ ፕሬዝደንት ዊሊያም ሩቶ ቢያስታውቁም፣ ዛሬ ሐሙስም ተቃውሞው ቀጥሎ፣ ፖሊስ የጎማ ጥይትና አስለቃሽ ጋዝ ሲትኩስ ውሏል።

SEE ALSO: በኬንያ የተፋፋመው የወጣቶች የታክስ ሕግ ተቃውሞ ቀጣናዊ አንድምታ

በአብዛኛው በወጣት ኬንያውያን የሚመራው ተቃውሞ ባለሥልጣናት ያልተዘጋጁበት ጉዳይ እንደሆነና የሩቶ መንግስትም በውይይት በመፍታት እና ተቃውሞውን በሃይል በመደፍጠጥ መካከል እንዲዋዥቅ አድርጎታል።

በደርዘን የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች በማዕከላዊው የናይሮቢ ክፍል ዛሬ ተሰባስበው የነበረ ሲሆን፣ ወታደሮች እና ፖሊሶች ወደ ሩቶ ቢሮ እና ፓርላማ የሚወስደውን መንገድ ዘግተዋል።

አነስ ያለ ቁጥር ወዳላቸው ተቃዋሚዎች አስለቃሽ ጭስ እና የጎማ ጥይት የተኮሱት ፖሊሶች፣ ሰባት የሚሆኑ ሰዎችንም ይዘዋል። አንዳንዶቹ ሰልፈኖች ወደ ፖሊስ ድንጋይ ሲወረውሩ እንዳስተዋለ የኤኤፍፒ ዜና ወኪል በዘገባው አመልክቷል።