የኢቫንካ ትረምፕ ጉብኝት

  • መለስካቸው አምሃ

ኢቫንካ ትረምፕ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ

ኢትዮጵያ ውስጥ ጉብኝት ላይ የሚገኙት የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትረምፕ ከፍተኛ አማካሪ እንዲሁም ልጃቸው ኢቫንካ ትረምፕ ዛሬ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ጋር ተገናኝተው ተነጋግረዋል።

ኢቫንካ ትራምፕ እና የልዑካን ቡድናቸው ሃገራቸው በኢትዮጵያ እየተወሰዱ ላሉት የማሻሻያ እርምጃዎች ያላትን ጠንካራ ድጋፍ በድጋሚ አረጋግጠዋል ብሏል ያሜሪካ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ።

ሚስ ትረምፕ በዛሬው ውሏቸው በቅድስት ሥላሴ መንበረ ፀባዖት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋኅዶ ቤተክርስትያን መሪ አባቶችና ሊቃውንት ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል።

ኢቫንካ ትረምፕ እዚያው ቅድስት ሥላሴ ባለፈው ወር ቢሾፍቱ አቅራቢያ በወደቀው ቦይንግ 737 ማክስ ኤይት ጄት አደጋ ለሞቱ 157 መንገደኞች ክብር ሰጥተው የአበባ ጉንጉንም አኑረዋል።

ሚስ ትረምፕ በተጨማሪም አዲስ አበባ ውስጥ የባሕላዊ ቡና ማስተናገጃ መደብር እና አንድ የጨርቃ ጨርቅ ማምረቻ ኩባንያም ጎብኝተዋል።

Your browser doesn’t support HTML5

የኢቫንካ ትረምፕ የጨርቃ ጨርቅ ማምረቻ ኩባንያ ጉብኝት

ኢቫንካ ትረምፕ ኢትዮጵያ የሚገኙት ፕሬዚዳንት ትረምፕ ባለፈው ወር ያስጀመሩትን በማደግ ላይ ያሉ ሃገሮች ሴቶችን የሥራ ዕድል ለማስፋት ያሰበ የሃምሣ ሚሊየን ዶላር ዕቅድ ለማስተዋወቅና ለማበረታታት እንደሆነ ተገልጿል።

ለዩናይትድ ስቴትስ መንግሥት ልዑካን የአፍሪካ ጉብኝት ከሚስ ትረምፕ ጋር የባሕር ማዶ የግል መዋዕለ ነዋይ ኮርፖሬሽን ኃላፊ ዴቪድ ቦሂጊያንም አብረው የተጓዙ ሲሆን አፍሪካ ውስጥ የሴቶችን ወሣኝነት ለማጠናከር የሚይግዝ በመቶዎች ሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ለማፍሰስ ማቀዱ ተነግሯል።

ኮርፖሬሽኑ ባወጣው መግለጫ “2x አፍሪካ” በሚባለው ዕቅድ አንድ ቢሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ መወሰኑንና 350 ሚሊየኑ በሴቶች ለተያዙና በሴቶች ለሚመሩ ንግዶች ቀጥተኛ መዋዕለ-ነዋይ ለማፍሰስ መታሰቡንም አስታውቋል።

ትላንት ከኢትዮጵያውያን ሴት ነጋዴዎች ጋር የተገናኙት ኢቫንካ ትራምፕ ሴቶችን ማገዝና የወሣኝነት ቦታቸውን መገንባት የብሄራዊ ፀጥታ ጥቅማችንን ያስጠብቃል ብለዋል።

ዝርዝሩን ከተያያዘው የድምጽ ፋይል ያዳምጡ

Your browser doesn’t support HTML5

የኢቫንካ ትረምፕ ጉብኝት