ብሊንከን በጋዛ እና በሊባኖስ ላለው ግጭት እልባት ፍለጋ ዛሬ እስራኤል ገቡ

  • ቪኦኤ ዜና

የዩናይትድ ስቴትሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንተኒ ብሊንከን

የዩናይትድ ስቴትሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንተኒ ብሊንከን የተቀዛቀዘውን የተኩስ አቁም ንግግር ለማነቃቃት፣ የተጠናከረ የሰብአዊ ርዳታ ወደ ጋዛ እንዲገባ ለማድረግ እና ብሎም በሊባኖስ በእስራኤል እና በሂዝቦላ መካከል እየተካሄደ ያለውን ጦርነት ለማርገብ በታለሙ ውጥኖች ዙሪያ ለመነጋገር ዛሬ ከእስራኤል መሪዎች ጋር ይገናኛሉ።

ብሊንከን የመስከረም 26ቱን የሃማስ ጥቃት ተከትሎ ጋዛ ውስጥ ግጭት ከተቀሰቀሰ ወዲህ 11ኛቸው በሆነው የመካከለኛው ምስራቅ ጉዟቸው ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና ከመከላከያ ሚኒስትራቸው ዮአቭ ጋላንት ጋራ ተገናኛተው ይነጋገራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ከተባሉት ንግግሮች ጥቂት ሰዓታት አስቀድሞ ሂዝቦላ በቴላቪቭ እና ሃይፋ አቅራቢያ በሚገኙ የእስራኤል ጦር ሠፈሮች ላይ ሮኬቶችን መተኮሱን ሲገልጽ፤ እስራኤል በበኩሏ ከሊባኖስ በኩል የተተኮሱትን ተወንጫፊዎች ማምከኗን አስታውቃለች።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛሬው ዕለት ቤይሩት ውስጥ ከሚገኘው ዋናው የመንግሥት ሆስፒታል አቅራቢያ እስራኤል በሰነዘረችው ጥቃት 13 ሰዎች ሲገደሉ፤ ሌሎች 57 መቁሰላቸውን የሊባኖስ የጤና ጥበቃ ሚንስቴር አስታውቀዋል።

በአንጻሩ የእስራኤል ጦር የቡድኑን የባሕር ኃይል ማዕከላዊ ጣቢያ ጨምሮ ቤይሩት ውስጥ በርካታ የሂዝቦላህ ዒላማዎችን መምታቱን ይፋ አድርጓል።