እስራኤል ሄዝቦላህ ላይ መጠነ ሰፊ ጥቃት አካሄደች

  • ቪኦኤ ዜና

በደቡባዊ ሊባኖስ ሰማይ ጭስ ይታያል

የእስራኤል ኃይሎች ዛሬ ሰኞ በደቡባዊ ሊባኖስ ሰፊ የአየር ድብደባ አካሂደዋል።

በእስራኤል እና በሄዝቦላህ ታጣቂዎች መካከል የተነሳው ግጭት ተባብሶ በቀጠለበት ወቅት የተካሄደው የአየር ድብደባ በቀጠናው ሰፊ ጦርነት እንዳይቀሰቅስ አስግቷል።

የአየር ድብደባውን ተከትሎ የእስራኤል ጦር ከ300 በላይ ዒላማዎች ላይ ጥቃት ማድረሱን ሲያስታውቅ ፣ የሊባኖስ መንግስት የዜና ማሰራጫ በበኩሉ፣ በደቡባዊው የሀገሪቱ ክፍል በሚገኙ በርካታ ቦታዎች ላይ ከባድ ጥቃቶች መፈጸማቸውን አስታውቋል።

የእስራኤል መከላከያ ኃይል ቃል አቀባይ ሪር አድሚራል ዳንኤል ሀጋሪ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የእስራኤል ኃይሎች እርምጃውን የወሰዱት ሄዝቦላህ ወደ እስራኤል ግዛት ለመተኮስ መዘጋጀቱን የሚያመለክቱ መረጃዎች በመገኘታቸው ነው ብለዋል።

ሀጋሪ አክለውም ሄዝቦላህ ሚሳይሎችን፣ ሰው አልባ አሮፕላኖችን እና ሌሎች የጦር መሳሪያዎችን ሲቪሎች በሚኖሩበት አካባቢ ማከማቸታቸውን ገልጸው፣ እስራኤል የሊባኖስ ዜጎች ሄዝቦላህ ከሚገኝባቸው አካባቢዎች ለቀው እንዲወጡ እየመከረች ነው ብለዋል።

ባለፉት ሳምንታት በእስራኤል እና በሊባኖስ ድንበር አካባቢ እየጨመረ የመጣውን ጦርነት ተከትሎ የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አዲስ የጉዞ ማስጠንቀቂያ አውጥቷል፡፡ የአሜሪካ ዜጎች የንግድ አውሮፕላኖችን በመጠቀም መውጣት እንዲጀምሩም አሳስቧል።