ከ20ሺሕ በላይ የራያ ወረዳዎች የግጭት ተፈናቃዮች ያለርዳታ ለወራት መቆየታቸውን ገለጹ

የኢትዮጵያ ካርታ

ባለፈው ሚያዝያ ወር የተቀሰቀሰውን ግጭት ተከትሎ ከኮረም፣ ወፍላ እና ዛታ ወረዳዎች፣ ወደ ዋግ ኽምራ እና የሰሜን ወሎ ዞኖች የተፈናቀሉ ሰዎች፣ ያለበቂ ሰብአዊ ድጋፍ ለሦስት ወራት መቆየታቸውን ተናገሩ። ተፈናቃዮቹ ጎዳና ላይ ከመተኛት ጀምሮ ለልመና መዳረጋቸውን ገልጸዋል።

Your browser doesn’t support HTML5

ከ20ሺሕ በላይ የራያ ወረዳዎች የግጭት ተፈናቃዮች ያለርዳታ ለወራት መቆየታቸውን ገለጹ

በአኹኑ ወቅር እርሳቸውም ተፈናቃይ መኾናቸውን የገለጹት እና ኮረም ከተማን ለሁለት ዓመት በከንቲባነት የመሩት አቶ ብርሃኑ ኀይሉም፣ ከሦስቱ ወረዳዎች የተፈናቀለው ሕዝብ ብዛት ከ22ሺሕ እንደሚልቅ ጠቅሰው፣ የምግብ አቅርቦቱ እጥረት አሳሳቢ መኾኑን አመልክተዋል፡፡

በርካታ ተፈናቃዮችን እንደተቀበለ የተገለጸው የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ተጠሪ ጽሕፈት ቤት በበኩሉ፣ ዞኑ ካለበት የሀብት ውስንነት ባሻገር፣ በአካባቢው ድርቅ በመከሠቱ ለተፈናቃዮቹ ሕይወት አድን ድጋፍ ለመስጠት መቸገሩን አስታውቋል፡፡

የዐማራ ክልል አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና ኮሚሽን፣ ለተፈናቃዮቹ የምግብ አቅርቦት ጥያቄ በቅርቡ ምላሽ እንደሚሰጥ አረጋግጧል፡፡