የሂዝቦላህ ምክትል ሃላፊ ቡድኑ የተኩስ አቁም ጥረቶችን ይደግፋል አሉ

  • ቪኦኤ ዜና

ፎቶ ፋይል፦ የሄዝቦላ ምክትል መሪ ናዒም ቃሰም

የሄዝቦላ ምክትል መሪ ናዒም ቃሰም በሊባኖስ እና እስራኤል ድንበር እየተባባሰ የመጣውን ግጭት ለማርገብ፤ “ሄዝቦላ የተኩስ አቁም መደረጉን ይደግፋል” ሲሉ በዛሬ ዕለት አስታውቀዋል፡፡

የሄዝቦላ ምክትል መሪ በቴሌቭዥን በተላለፈው ንግግራቸው፤ የሊባኖስ ፓርላማ አፈ- ጉባዔ ናቢህ በሪ ጦርነቱን ለማስቆም ያደረጉትን ሙከራ ጠቅሰዋል፡፡ ይሁን እንጂ እስራኤል ዛሬ ማክሰኞ በደቡብ ምዕራብ ሊባኖስ አዲስ የምድር ጦር ጥቃት ያወጀች ሲሆን በቤይሩት በዳሂህ አካባቢ የአየር ድብደባ ማድረጓን ቀጥላለች፡፡

ቃሰም አክለውም ሂዝቦላህ በተደራጀ ሁኔታ “አሰቃቂ ድብደባዎችን” ተወጥቷቸዋል ብለዋል፡፡

ከስምንት ቀናት በፊት እስራኤል በሊባኖስ ላይ መውሰድ የጀምረቸው የምድር ጦር ጥቃትን ‘የተገደበ፣ በአንድ አካባቢ የተወሰነ እና ዒላማ ያለው ተልዕኮ’ ነው ስትል ብላለች፡፡

የእስራኤል ጦር በዛሬው የአየር ድብደባ የሄዝቦላ የጦር መሪ እና በሊባኖስ እና በኢራን መካከል በሚደረገው የጦር መሳሪያ ልውውጥ ተሳታፊ የሆነውን ሱሄል ሁሴኒን መግደሉን አስታውቋል፡፡

በአጸፋው ሄዝቦላ በሰሜናዊ እስራኤል ሃይፋ ከተማ ላይ ሮኬቶችን መተኮሱን ሲገልጽ እስራኤል በበኩሏ በርካታ ሮኬቶችን አምክኛለሁ ብላለች፡፡