የዓለም አቀፍ የጤና ባለስልጣናት ጊኒ ከኢቦላ ነጻ መሆኗን አወጁ

  • ቆንጂት ታየ

በጊኒ ኮናርኪ የኢቦላ ቫክሲን ሲሰጥ [ፎቶ - አሶሽየትድ ፕረስ/AP]

“እነሆ ጊኒ ከኢቦላ ነጻ ሆነች” ሲሉ ዓለም ኣቀፍ የጤና ባለስልጣናት ኣወጁ። በዚያች የምዕራብ ኣፍሪካ ሃገር ኢቦላ ከሁለት ሺህ ኣምስት መቶ የሚበልጡ ሰዎች መግደሉ ይታወሳል።

አሁን ጊኒ ከወረርሺኙ ተገላገለች በመባሉ ለዚሁ ለመብቃት የምትጠባበቀው ላይቤሪያ ብቻ ትሆናለች።

የዓለም ባንክ ፕሬዚደንት ጂም ዮንግ ኪም ባወጡት የደስታ መግለጫ… የጊኒን ህዝብና መንግስት እንኩዋን ደስ ያላችሁ ካሉ በሁዋላ በዚሁ ኣንድም የበሽታው ተጠቂ በሌለበት ሁኔታ ለመዝለቅ ነቅታችሁ ተጠባባቁ ሲሉ መክረዋል።

ነገ ረቡዕ ጊኒ ዋና ከተማ ኮናክሪ ላይ ይፋ ስነ ስርዓት ይካሄዳል።

ባለፈው ህዳር በጊኒ የመጨረሻዋ የምትታወቅ የኢቦላ ታማሚ የነበረችው ሁለት ዓመት ያልሞላት ህጻን ኮናክሪ በሚገኝ የህክምና ማዕከል ታክማ መዳኑዋ ይታወሳል።

በሀገሪቱ ኣሁንም በቫይረሱ የመጠቃት ምልክት ያሳዩ እንደሆን ክትትል እየተደረገላቸው ያሉ በርካታ ሰዎች ያሉ ሲሆን ኣንድም ባለመገኘቱ ነው ከኢቦላ ነጻ ተብሎ የታወጀላት። ዘገባውን ለማዳመጥ የድምጽ ፋይሉን ይጫኑ።

Your browser doesn’t support HTML5

የዓለም አቀፍ የጤና ባለስልጣናት ጊኒ ከኢቦላ ነጻ መሆኗን አወጁ