በጦርነት በምትታመሰው ሱዳን የኮሌራ በሽታ እየተስፋፋ ነው

  • ቪኦኤ ዜና

ፎቶ ፋይል፦ በሱዳን ምስራቃዊ ሱዳን ካሳላ ግዛት ዋድ አል-ሂሉ ውስጥ ኮሌራ ህሙማን የሚታከሙበት በገጠር ማገገሚያ መአከል

በጦርነት በምትታመሰው ሱዳን የኮሌራ በሽታ እየተስፋፋ መሆኑን እና ባለፉት ሁለት ወራት ውስጥ ብቻ ቢያንስ 388 ሰዎች ህይወታቸው ሲያልፍ ወደ 13 ሺህ የሚጠጉ ለህመም መዳረጋቸውን የጤና ባለሙያዎች አስታውቀዋል።

በሽታው በተለይ በጦርነቱ የተፈናቀሉ በሚሊየኖች የሚቆጠሩ ሰዎች በሚገኙበት ምስራቃዊው የሱዳን ክፍል በቅርቡ በጣለው ከባድ ዝናብ እና ጎርፍ መባባሱም ተጠቁሟል። የሱዳን ጤና ሚኒስቴር እሁድ እለት ባወጣው ሪፖርት፣ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ብቻ በኮሌራ ጉዳት የደረሰባቸው ስድስት ሰዎች መሞታቸውን እና 400 ያክል መታመማቸውን ግልጿል።

እ.አ.አ በ2017 ዓ.ም በሱዳን ተከስቶ በነበረ የኮሌራ ወረርሽኝ ቢያንስ 700 ሰዎች ሲሞቱ ወደ 22 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች ከሁለት ወራት ባነሰ ጊዜ ውስጥ በበሽታው ተጠቅተው ነበር።