በመንግሥት ኃይሎች እና የፋኖ ታጣቂዎች ዳግም ግጭት ነዋሪዎች እንደተጎዱ ተገለጸ

Your browser doesn’t support HTML5

በመንግሥት ኃይሎች እና የፋኖ ታጣቂዎች ዳግም ግጭት ነዋሪዎች እንደተጎዱ ተገለጸ

በዐማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን ቆቦ ወረዳ፣ ባለፈው ማክሰኞ፣ በመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች እና በፋኖ ቡድን ታጣቂዎች መካከል፣ በድጋሜ ባገረሸው ግጭት፣ የሰዎች ሕይወት እንዳለፈ ተገለጸ፡፡

የአካባቢው የዐይን እማኞች ለአሜሪካ ድምፅ እንደገለጹት፣ ግጭቱን ተከትሎ፣ ከትላንት በስቲያ ቅዳሜ ጀምሮ፣ የንግድ ቤቶች እና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እስከ ዛሬ ሰኞ ድረስ እንደተዘጉ ናቸው፡፡

በሌላ በኩል፣ በክልሉ፣ በምዕራብ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች፣ በመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች እና በፋኖ ቡድን ታጣቂዎች መካከል በቀጠለው ግጭት፣ ተቋርጠው የነበሩ የስልክ አገልግሎቶች፣ ካለፈው ቅዳሜ እኩለ ለሊት ጀምሮ እንደተከፈቱ፣ የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡

የስልክ አገልግሎቱ ለሦስት ሳምንት ተቋርጦ እንደቆየ የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ በከተሞቹ፣ ከባለሦስት እግር ባጃጅ ውጭ፣ የታክሲም ኾነ የሀገር አቋራጭ የትራንስፖርት አገልግሎት እንዳልተጀመረ ገልጸዋል፡፡

ዛሬ ሰኞ በተካሔደው 6ኛው የሁለቱ ምክር ቤቶች 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን የመክፈቻ ሥነ ሥርዐት ላይ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ፣ በዐማራ ክልል ያለውን ግጭት በቀጥታ ባይጠቅሱም፣ ልዩነቶችን በሰላም መፍታት እንደሚገባ አስረድተዋል።

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ይከታተሉ።