በመርካቶው የእሳት አደጋ በሰውና ንብረት ላይ ጉዳት ደረሰ

አዲስ አበባ መርካቶ ሸማ ተራ የተከሰተው እሳት

Your browser doesn’t support HTML5

በመርካቶው የእሳት አደጋ በሰውና ንብረት ላይ ጉዳት ደረሰ

ትላንት ጥቅምት 11 ቀን 2017 ዓ.ም. አዲስ አበባ መርካቶ ውስጥ በደረሰው የእሳት አደጋ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን፣ የከተማዋ እሳት እና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። መርካቶ “ሸማ ተራ” በሚባለው አካባቢ የደረሰውን የእሳት አደጋ ለማጥፋት ስድስት ሰዓታት መፍጀቱን፣ የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ አቶ ንጋቱ ማሞ ለቪኦኤ ገልጸዋል።

ከአደጋው ጋራ በተያያዘ በሰባት ሰዎች ላይ ቀላልን በሁለት ሰዎች ላይ ደግሞ ከባድ ጉዳት መድረሱን የአዲስ አበባ ፖሊስ ዛሬ በአወጣው መግለጫ አስታውቋል። የከተማዋ እሳት እና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በእሳት አደጋው የሞተ ሰው እንደሌለ የተናገሩት የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ አቶ ንጋቱ በበኩላቸው፣ የአደጋው መንስኤ ምን እንደሆነ ፖሊስ በማጣራት ላይ መሆኑን አመልክተዋል።

እሳቱ በአካባቢው በፍጥነት በመዛመቱ፣ ጉዳቱን ጨምሮታል ያሉት አቶ ንጋቱ፣ አደጋውን ለመቆጣጠር ስድስት ሰዓታት የፈጀ ጥረት መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የነበሩት ኹኔታዎች የእሳት ማጥፋት ሥራውን አስቸጋሪ እንዳደረጉትም ገልፀዋል፡፡

የእሳት ማጥፋት ሥራው፣ ከአዲስ አበባ እሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አቅም በላይ ሆኖ እንደነበር አቶ ንጋቱ ማሞ ጠቅሰው፣ ተቋሙ የሌሎችን ድጋፍ በመጠየቁ በተለያዩ አካላት ትብብር በቁጥጥር ስር መዋሉን አስታውቀዋል፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ የእሳት አደጋውን መንስኤ ለማጣራት ከፌዴራል ፖሊስ ጋራ በመተባበር የምርመራ ሥራ መጀመሩን ገልፆዋል፡፡ አደጋውን እንደ ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም የስርቆት ወንጀል የፈፀሙ 33 ተጠርጣሪዎችን ይዞ እየመረመረ እንደሆነም አመልክቷል፡፡ የአሜሪካ ድምፅ፣ ወደ አካባቢው ተንቀሳቅሶ፣ ኹኔታውን ለመመልከትና ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች ለማነጋገር ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ ከሰሞኑ የሚመለከታቸውን ኃላፊዎች በማስፈቀድና በአካባቢው ያሉ ተጎጅዎችን በማነጋገር ሰፋ ባለ ዘገባ እንመለሳለን፡፡