በዐዲስ አበባ የኤርትራ ስደተኞች እስር እንዲቆምና ምዝገባ እንዲጀመር ኢሰመኮ ጠየቀ

Your browser doesn’t support HTML5

በዐዲስ አበባ የኤርትራ ስደተኞች እስር እንዲቆምና ምዝገባ እንዲጀመር ኢሰመኮ ጠየቀ

በዐዲስ አበባ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎች፣ “የማስረጃ ሰነድ የላችኹም፤” በሚል ምክንያት እየታሠሩ እንደኾነ ያስታወቀው፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን፣ እስሩ እንዲቆምና የተቋረጠው የስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎች ምዝገባ እንዲጀመር ጠየቀ፡፡

በጉዳዩ ላይ ክትትል ማድረጉን የጠቀሰው ኮሚሽኑ፣ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች፣ “የማስረጃ ሰነድ የላችኹም፤ ያለፈቃድ ነው የምትሠሩት” በሚሉ ምክንያቶች፣ ለእስር የተዳረጉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኤርትራውያን ስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎች መኖራቸውን ገልጾ፣ ከመካከላቸውም ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋሉና ክሥ ሳይመሠረትባቸው በእስር የቆዩ መኖራቸውን ተመልክቻለኹ፤ ብሏል። የዘፈቀደ እስሩ ሊቆም እንደሚገባም አሳስቧል፡፡

በመግለጫው ላይ፣ ለአሜሪካ ድምፅ ማብራሪያ የሰጡት የኮሚሽኑ የሥራ ሓላፊ አቶ ሱራፌል ድንቅዓለም፣ ችግሩን ለመፍታት፣ ለሁለት ዓመታት ተቋርጦ የቆየው፣ የስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎች ምዝገባ፣ በአፋጣኝ እንዲጀመር ጥሪ አቅርበዋል፡፡