በዐማራ ክልል በምዕራብ ጎጃም ዞን ልዩ ልዩ ወረዳዎች ግጭቶች እንደቀጠሉ ነው

Your browser doesn’t support HTML5

በዐማራ ክልል በምዕራብ ጎጃም ዞን ልዩ ልዩ ወረዳዎች ግጭቶች እንደቀጠሉ ነው

በዐማራ ክልል በምዕራብ ጎጃም ዞን በተለያዩ ወረዳዎች፣ በመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች እና በፋኖ ቡድን ታጣቂዎች መካከል፣ ለሳምንታት ጋብ ብሎ የቆየው ግጭት፣ ካለፈው ሳምንት ቅዳሜ ጀምሮ ዳግም ተባብሶ እንደቀጠለ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡

ከአሜሪካ ድምፅ ጋራ ዛሬ ቆይታ ያደረጉት፣ በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢ ጠህናን፣ የደጋ ዳሞት፣ ቡሬ ደምበጫ ፈረስ ቤት እና ቋሪት ወረዳ ነዋሪዎች፣ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ የተጀመረው ግጭት፣ እስከ ዛሬ ድረስ እንደቀጠለ ተናግረዋል፡፡

ለግጭቱ መቀስቀስ እንደ ምክንያት የጠቀሱትም፣ የመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች፣ በየአካባቢው ከጀመሩት የቤት ለቤት ፍተሻ ጋራ ተያይዞ የመብቶች ጥሰት በመፈጸሙ ነው፤ ብለዋል፡፡

ዛሬ፣ ለአራተኛ ቀን የቀጠለውን ግጭት ተከትሎ፣ በየአካባቢው የንግድ እና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እንደተዘጉ መኾናቸውን፣ ነዋሪዎቹ አክለው ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል፣ በዐማራ ክልል ሰሜናዊ ዞኖች፣ በመከላከያ ኀይሉ እና በፋኖ ታጣቂ ቡድን መካከል የተቀሰቀሰው ዐዲስ ጦርነት፣ በላሊበላ ከተማ የሚገኘውን የላሊበላ ውቅር አብያተ መቅደሶች፣ አደጋ ላይ ጥሏል፤ የሚል ስጋት በነዋሪዎች ዘንድ ፈጥሯል፤ ሲል ሮይተርስ ዘግቧል።

የመንግሥት ኮምዩኒኬሽንስ አገልግሎት ሚኒስትሩ፣ በቅርቡ በሰጡት መግለጫ፣ የዐማራ ክልል የሰላም ኹኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እንደተሻሻለ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

ዝርዝር ዘገባውን ከተያያዘው ፋይል ይከታተሉ፡፡