በሆሩ ጉድሩ የሰላማዊ ሰዎች ግድያ

Your browser doesn’t support HTML5

በሆሩ ጉድሩ የሰላማዊ ሰዎች ግድያ

በኦሮምያ ክልል፣ ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች በሦስት ሳምንታት ውስጥ ብቻ በተፈጸሙ ጥቃቶች ከ100 በላይ ሲቪል ሰዎች ተገለዋል ሲል የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ገለጸ።

ኮሚሽኑ ትናንት መስከረም 16 ባወጣው መግለጫ፣ ተከታታይ ጥቃቶችን የፈጸሙት ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ብሎ የሚጠራው እና የኢትዮጵያ ፓርላማ ሸኔ በሚል በአሸባሪነት የፈረጀው ቡድን እንደዚሁም የአማራ ኢ-መደበኛ ታጣቂዎች ናቸው ብሏል።

በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን በአሙሩ እና ጃርደጋ ጃርቴ ወረዳዎች ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በተፈጸሙ ጥቃቶች በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን የተለያዩ ማኅበረሰቦች አአባላት የሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎችም ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ቅዳሜ መስከረም 14 ባወጣው መግለጫ፣ “ሸኔ” ሲል የገለጸው ታጣቂ ቡድን በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን ጃርደጋ ጃርቴ በሚገኙ ንጹሃን ላይ ግድያ መፈጸሙን አመለክቷል፡፡

ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ብሎ የሚጠራው እና በመንግሥት ሸኔ በመባል የሚታወቀው ታጣቂ ደግሞ፣ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ግድያ ፈጽሟል በሚል የቀረቡበትን ውንጀላዎች አስተባብሏል፡፡

የአማራ ኢ-መደበኛ ታጣቂዎች በሚል የተገለጹትን በተመለከተ ግን እስካሁን ምላሽ የሰጠ አካል የለም።