በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ኢትዮጵያና ኤርትራ በሰብዓዊ መብቶች አያያዛቸው ተወቀሱ


የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የ2012 ዓ.ም የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት - ዌብ ሣይት
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የ2012 ዓ.ም የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት - ዌብ ሣይት

በኢትዮጵያና ኤርትራ ውስጥ የዜጎች ነፃነቶች ጉዳይ አሣሣቢ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው ዓመታዊ ሪፖርቱ አስታወቀ፡፡




የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት


please wait

No media source currently available

0:00 0:06:24 0:00
ቀጥተኛ መገናኛ

በኢትዮጵያና ኤርትራ ውስጥ የዜጎች ነፃነቶች ጉዳይ አሣሣቢ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው ዓመታዊ ሪፖርቱ አስታወቀ፡፡

ሪፖርቱ ኢትዮጵያን በተለይ የተመለከታት ፀረ-ሽብር ሕጓን ጋዜጠኞችን ለማሣደድ ጉዳይ የተጠቀመችበት መሆኗን ገልፆ በዓመቱ ውስጥ ጋዜጠኞቹ ውብሸት ታየ፣ ርዕዮት ዓለሙ እና እስክንድር ነጋ የተከሰሱትና የተፈረደባቸው ፀረ-ሽብር አዋጁን ተላልፋችኋል ተብለው መሆኑን አመልክቷል፡፡

ሌሎች ስድስት ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፅሁፍ አውጭዎች ወይም ብሎገሮች በሌሉበት ጥፋተኝነት የተበየነባቸው መሆኑን በአጠቃላይም የተቃዋሚ ፓርቲዎች አባላትና የፖለቲካ ተዋንያንን ጨምሮ 31 ሰዎች በዚሁ ሕግ የተፈረደባቸው መሆኑን ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ የዘፈቀደ ግድያዎች መፈፀማቸውን፣ በእሥረኞች ላይ የሥቃይ አድራጎትና አያያዝ መከናወኑን፣ በትምህርት ሂደት ነፃነት ላይ ገደቦች መጣላቸውንና በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መገባቱን ሪፖርቱ አትቷል፡፡

ሂላሪ ሬነር - የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃልአቀባይ
ሂላሪ ሬነር - የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃልአቀባይ
የኢትዮጵያ መንግሥት በተለይ በሃይማኖት ጉዳዮች ውስጥ ጣልቃ የመግባቱ ነገር ዩናይትድ ስቴትስን ከዕለት ወደዕለት ይበልጥ እያሳሰባት መምጣቱን የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ቃልአቀባይ ሂላሪ ሬነር ገልፀዋል፡፡

ኤርትራን የሚመለከተው የሪፖርቱ ክፍል በሃገሪቱ ውስጥ በፀጥታ ኃይሎች ከሕግ ውጭ የሆኑ ግድያዎች መፈፀማቸውን፣ በተያዙ ሰዎች ላይ የጭካኔ አድራጎት መከናወኑን፣ የእሥር ቤቶቹ አያያዝ እጅግ የከፋ መሆኑን፣ እሥረኛ ብቻውን ተነጥሎ ለተራዘመ ጊዜ እንዲከለል እንደሚደረግ፣ እነዚህ የእሥር ሁኔታዎች አንዳንዴም በእሥረኞች ላይ ሞት ማድረሣቸውን ይዘረዝራል፡፡

ሪፖርቱ አክሎም የአሥመራ መንግሥት በሲቪል ነፃነቶች ላይ ከባድ ክልከላና ዕገዳዎችን መጣሉን፣ ይህም ሃሣብን በመግለፅ ወይም በመናገር፣ በመፃፍና በዕምነት ነፃነቶች ላይ የተጣሉ ገደቦችን እንደሚጨምር ገልጿል፡፡

በኤርትራ እሥር ቤቶች ውስጥ ከአምስት ሺህ እስከ እሥር ሺህ የሚደርሱ እሥረኞች እንደሚገኙ አንዳንድ ግምቶች እንደሚጠቁሙ የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርቱን የተንተራሰው የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ቃልአቀባይ ማብራሪያ አመልክቷል፡፡

እስከአሁን ከኢትዮጵያም ይሁን ከኤርትራ በዚህ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ሠነድ ላይ የተሰጠ ምላሽ ወይም አስተያየት የለም፡፡
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት

ለተጨማሪና ዝርዝር መረጃ ከላይ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡

http://www.state.gov/j/drl/rls/hrrpt/humanrightsreport/
ይህ ማገናኛ ወደ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ዌብ ሣይት የ2012 የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት ይወስድዎታል፡፡
XS
SM
MD
LG