በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በደቡብ ኦሞ የአሪ እና ሙርሲ ጎሣዎች ግጭት አምስት ሰዎች ተገደሉ


በደቡብ ኦሞ የአሪ እና ሙርሲ ጎሣዎች ግጭት አምስት ሰዎች ተገደሉ
please wait

No media source currently available

0:00 0:01:58 0:00

በኢትዮጵያ የደቡብ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን ደቡብ አሪ እና ሰላማጎ ወረዳ፣ በአሪ እና በሙርሲ ጎሣዎች መካከል፣ በመሬት ይገባናል እና ከብት በመዘራረፍ በተቀሰቀሰ ግጭት፣ አምስት ሰዎች መገደላቸውን፣ ነዋሪዎች ለአሜሪካ ድምፅ ተናገሩ።

የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ በሁለት ጎሣዎች መካከል በተፈጸመ የከብት ዝርፊያ የተቀሰቀሰው ግጭት፣ የአምስት ሰዎችን ሕይወት ቀጥፏል፤ ሲሉ ለአሜሪካ ድምፅ አረጋግጠዋል።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁን ግጭቱ የተፈጠረበት የጨለጎዳ ቀበሌ ነዋሪ፤ በሁለቱ ጎሣዎች መካከል በከብት ዝርፊያ የተነሣ በተከፈተው የእርስ በርስ ግጭት የደረሰው ጉዳት ከፍተኛ መኾኑን ገልጸዋል፡፡

ግጭቱ ሦስተኛ ቀኑን ማስቆጠሩን የሚናገሩት እኚኹ ነዋሪ፣ እስከ አሁን ወደ አካባቢው የደረሰ የመንግሥት ጸጥታ ኃይሎች አለመኖሩንና ግጭቱ ዛሬም መቀጠሉን አመልክተዋል።

ሌላው ነዋሪ አቶ ዳንኤል ዎያዮ፣ በሰላማጎ በሚኖሩ በሙርሲ እና በደቡብ አሪ ወረዳ ውስጥ፣ በአሪ ጎሣዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የተገደሉትን ሰዎች እንደሚያውቋቸው በመጥቀስ፣ በስም ዘርዝረው ተናግረዋል።

የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ንጋቱ ድንሳ፣ በአሪ እና በሙርሲ ጎሣዎች መካከል ግጭት መፈጠሩን ገልጸው፣ ሰዎች ለኅልፈተ ሕይወት መዳረጋቸውንም አስታውቀዋል።

በአሁኑ ወቅት፣ የመንግሥት ጸጥታ ኃይሎች ወደ አካባቢው መድረሳቸውንና ግጭቱን ማስቆማቸውን፣ አቶ ንጋቱ ተናግረዋል።

ከትላንት ወዲያ በዚኹ ዞን ሰላማጎ ወረዳ፣ በቦዲ እና በዲሜ ጎሣዎች መካከል በተነሣ ግጭት፣ 11 ሰዎች መገደላቸውን፣ የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ለአሜሪካ ድምፅ መግለጹ ይታወሳል፡፡

XS
SM
MD
LG