በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ድርቁ ህፃናትን በብርቱ እየጎዳ ነው


ድርቁ ህፃናትን በብርቱ እየጎዳ ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:02:14 0:00

ድርቅ አብዝቶ እያጠቃቸው በሚገኙ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በአሥር ሺሆች የሚቆጠሩ ህፃናት "ለሞት በሚዳርግ ደረጃ "ሲል የብሪታኒያ ግብረ ሰናይ ድርጅት ህፃናት አድን በገለፀው የምግብ እጥረት ብርታት እየተሰቃዩ መሆኑን አስታውቋል።

በአፍሪካ ቀንድ የሰፋ አካባቢ ዝናብ በአራት ተከታታይ መደበኛ ወቅቶች አለመጣሉ ኢትዮጵያ፣ ኬንያና ሶማሊያ ውስጥ በአርባ ዓመታት ደርሶ በማያውቅ ብርታት የከፋ የረሃብ ቀውስ ማስከተሉን አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል።

በዘንድሮውም የክረምት ወቅት በቂ ዝናብ አይጥልም ተብሎ ተተንብይዋል።

የብሪታንያው ግብረ ሰናይ ድርጅት “ሴቭ ዘ ቺልድረን” ወይም “ህፃናት አድን” ባወጣው ሪፖርት ኢትዮጵያ ውስጥ በኦሮምያ፥ በደቡብ፥ በሶማሌና በደቡብ ምዕራብ ክልሎች ከአንድ ሚሊዮን የሚበልጥ ሰው አጣዳፊ የምግብ ዕርዳታ እንደሚያስፈልገው ገልጿል።

“አንድ መቶ ሰማኒያ አምስት ሺህ የሚሆኑ ህፃናት ለሞት በሚዳርግ ደረጃ በከፋ ረሃብ እየተሰቃዩ ናቸው”ም ብሏል ድርጅቱ።

ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉት የተለያዩ ቀውሶች ግንባር ቀደምና ከሁሉም በላይ ተጎጂዎቹ ህፃናቱ መሆናቸውን የድርጅቱ የኢትዮጵያ ቢሮ ዳይሬክተር ዣቪየር ዩቤር ተናግረዋል።

“በግጭቶችና ላለፉት ሁለት ዓመታትም በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት አብዝቶ የተጎዳውን አቅማቸውን የተራዘመው ከባድ ድርቅ ይበልጥ አዳክሞታል ብለዋል ዩቤር።

በድርቁ እጅግ ከተጎዱት አንዱ በሆነው በሶማሌ ክልል ባለፈው ዓመት የምግብ ዕጥረት ምጣኔው ወደ ስድሳ አራት ከመቶ ማሻቀቡን የህፃናት አድን ድርጅት መግለጫ አክሎ ጠቁሟል።

በዚሁ ጊዜ ውስጥ ህይወታቸውን የሚያተርፍ ህክምና በሚያስፈልጋቸው ደረጃ እጅግ ከባድና አጣዳፊ ጣልቃ ገብነት በሚያስፈልገው ረሃብ የተጎዱ ከሃምሳ ሺህ የሚበልጡ ህፃናትን መመዝገቡንም ድርጅቱ ገልጿል።

በህዝብ ብዛት ከአፍሪካ ሁለተኛ በሆነችውና በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል በተካሄደው ጦርነት በተጎዳችው ኢትዮጵያ በተራዘመው የከበደ ድርቅ ከስምንት ሚሊዮን በላይ ህዝቧ መጎዳቱን የኤኤፍፒ ዘገባ አውስቷል።

ሰላሳ ሚሊዮን ህዝብ ሰብዓዊ እርዳታ ጠባቂ መሆኑን ሴቭ ዘ ቺልድረን በዚሁ መግለጫው አመልክቷል።

የምግብና የነዳጅ ዋጋ መናርን ያስከተለው የዩክሬኑ ጦርነት ችግሩን እንዳባባሰው ዘገባው አመልክቶ በሰብዓዊ ዕርዳታ ተማፅኖም በቂ ገንዘብ አለመገኘቱን ገልጿል።

የዓለም የምግብ ፕሮግራም ባለፈው የካቲት ለለጋሾች ካቀረበው ጥያቄ እስካሁን ያገኘው አራት ከመቶውን ብቻ መሆኑን አስታውቋል።

/ዘገባው የአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ነው/

XS
SM
MD
LG