በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የአውሮፓ ኅብረት መሪዎች አዲስ ዕቅድ የስደተኞች አሳዛኝ ሁኔታ ትንሽ ሊቀይር ይችላል


የአውሮፓ ኅብረት መሪዎች አዲስ ዕቅድ የስደተኞች አሳዛኝ ሁኔታ ትንሽ ሊቀይር ይችላል
please wait

No media source currently available

0:00 0:02:11 0:00

ከአንድ ሳምንት በፊት አንድ የዓሣ ማስገሪያ መርከብ ከአምስት መቶ በላይ ፍልሰተኞችን እንደያዘ በሜዲትሬኒያን ባህር ላይ ከሰመጠ በኋላ፤ በሕይወት ከሚገኙት ይልቅ፣ አስከሬኖች ይበልጥ በመገኘታቸው፣ የአደጋ ሥራው መዳከም አሳይቷል።

የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዚደንት ኧርሰላ ቮን ደር ላየን በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሰጥተዋል። ነገ ሐሙስም የአውሮፓ ሕብረት መሪዎች በቮን ደር ላየን ዕቅድ ላይ ይወያያሉ።

የኮሚሽኑ ዋና መሥሪያ ቤት በሚገኝበት በብራስልስ ቢሯቸው በዜና ሰዎች የተጠየቁት ኧርሰላ ቮን ደር ላየን፣ “የተፈጠረው ነገር አስደንጋጭ ነበር፣ በአስቸኳይ ወደ እርምጃ መግባት አለብን” ሲሉ ተደምጠዋል።

ቮን ደር ላየን እንደሚሉት፣ ትኩረቱ መሆን የነበረበት፣ ወደ አውሮፓ ለመዝለቅ የሚሹ ፍልስተኞች መነሻ የሆነችውን የቱኒዚያ ባለሥልጣናትን ማገዝ ነበር። ኢኮኖሚዋን ማረጋጋት እና ለረጅም ግዜ ሲጠበቅ የነበረውን የአውሮፓ ሕብረት የጥገኝነት መጠየቂያ ደንብ ማሻሻያን ማጠናቀቅ ነው ሲሉም አክለዋል።

የቮን ደር ላየን ምላሽ፣ ከእርሳቸው ቀደም ብሎ የኮሚሽኑ ፕሬዚደንት ከነበሩት ሆዜ ማኑኤል ባሮሶ፣ በተመሳሳይ በእ.አ.አ 2013 ለተፈጠረ አደጋ ከሰጡት ተግባራዊ ምላሽ በተቃራኒ የቆመ ነው። ባሮሶ፣ “እንዲህ ዓይነት አደጋ ሁለተኛ አይደገምም” ሲሉ፣ የጣሊያን ባህር ኃይል ደግሞ፣ የፍለጋ እና የነፍስ አድን ቡድን አቋቋመ። የነፍስ አድን ሥራው ፍልሰተኞችን የበለጠ ወደ አውሮፓ እንዲሳቡ ያደርጋል በሚል፣ ከአንድ ዓመት በኋላ እንዲቆም ተደረገ። ከዛ ወዲህ ፍልሰተኞች ይበልጥ ወደ አውሮፓ ለመጓዝ እንዳይበረታቱ በሚል፣ ኅብረቱ በፍልሰተኞች ላይ የሚደርሰውን አደጋ በተመለከተ ምንም ሳያደርግ ቆይቷል።

የአውሮፓ ኅብረት መሪዎች፣ ነገ ሃሙስ በቮን ደር ላየን ዕቅድ ላይ ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።እንደ ኦስትሪያ፣ ሃንጋሪ፣ እና ፖላንድ የመሰሉ አገራት ፍልሰተኞችን በጋራ የመቀበልን ሃሳብ ስለማይደግፉ፣ ዋናው ትኩረት የሚሆነው ፍልሰተኞች ቀድሞውንም እንዳይገቡ መከላከል በሚለው ላይ ነው።

ቮን ደር ላየን ለመሪዎቹ በላኩት ደብዳቤ፣ “ፍልሰተኞችን ከመነሻቸው አፍሪካ እና ቱርክ ላይ ማስቆም፣ ሕገ ወጥ ዝውውርን መዋጋትና እንዲሁም መሸጋገሪያ ከሆኑት አገራት ጋር አብሮ በመሥራት ፍልሰተኞቹ እንዳይነሱ ወይም እንዳይሻገሩ ማድረግ” የሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርገዋል።

በዚህ ዓመት ከጥር እስከ ግንቦት ወራት ባሉት ግዜ ውስጥ ብቻ፣ 50 ሺህ 300 ፍልሰተኞች አውሮፓ ገብተዋል። ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ግዜ ጋር ሲነጻጸር፣ ከእጥፍ በላይ መሆኑን ፍሮንቴክስ የተባለውና ጉዳዩን የሚከታተለው ተቋም አስታውቋል።

XS
SM
MD
LG