በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በካሜሩን ባህላዊ መሪው ከ18 ወራት እገታ በኋላ ተለቀቁ


በካሜሩን ባህላዊ መሪው ከ18 ወራት እገታ በኋላ ተለቀቁ
please wait

No media source currently available

0:00 0:01:35 0:00

የጸጥታ ችግር ባልተለየው ሰሜን ምዕራብ ካሜሩን፣ ለ18 ወራት በተገንጣዮች ታግተው የነበሩ ባህላዊ መሪ፣ ትላንት ኀሙስ። መንግሥት እንደሚለው፣ ባህላዊ መሪው ፎን ሹሚታንግ የተለቀቁት፣ ከተገንጣዮቹ ጋራ ከተደረገ ውጊያ በኋላ ነው። ተገንጣዮቹ ግን፣ በራሳቸው ፈቃድ እንደለቀቋቸው ነው የሚናገሩት።

ታግተው የነበሩትን ባህላዊ መሪ፣ የአገሪቱ ጦር በውጊያ ማስለቀቁን፣ እንዲሁም በርካታ የተገንጣዩ ቡድን ወታደሮች መገደላቸውን፣ የካሜሩን መንግሥት ይገልጻል።

ባህላዊ መሪውን ማስለቀቅ መቻላቸው፣ በተገንጣዮች ምክንያት ለዓመታት ሁከት ያልተለየውን የአገሪቱን ክፍል፣ ቀስ በቀስ በቁጥጥር ሥር እያደረጉ መምጣታቸውን እንደሚያመለክት፣ ባለሥልጣናት በመናገር ላይ ናቸው።

ባህላዊ መሪው ሹሚታንግ፣ ራሳቸውን ‘ጀኔራል ኖ ፒቲ’ ብለው በሚጠሩት የተገንጣዮቹ መሪ የታገቱት፣ ባለፈው ታኅሣሥ ወር ነበር።

ከተገንጣይ ቡድኖቹ አንዱ የኾነው፣ የአምባዞኒያ ሕዝቦች መብት ተቆርቋሪ ቡድን መሪ የኾኑት ካፖ ዳንኤል፣ ባህላዊ መሪው፥ ከአምስት ወራት ድርድር በኋላ እንደተለቀቁ ይናገራሉ።

“የካሜሩን መንግሥት፣ 15 የሚኾኑ የ ኖ ፒቲ ቤተሰቦችን፣ ባለፈው ታኅሣሥ ያዘ። ይህ የተደረገው፣ ኖ ፒቲ፣ ተገዶ ወደ ድርድር እንዲገባና ባህላዊ መሪው እንዲለቀቁ ለማድረግ ነው። የኾነውም ያ ነው። ምንም ዐይነት ወታደራዊ ዘመቻ አልነበረም። ባህላዊ መሪው ከተለቀቁ በኋላ፣ ለካሜሩን ባለሥልጣናት ተሰጡ፤” ብለዋል ካፖ ዳንኤል።

የካሜሩን መንግሥት፣ ባህላዊ መሪው በድርድር እንደተለቀቁ በአጋቾቹ መገለጹን ያስተባብላል።

ዳንኤል ጨምረው እንዳሉት፣ ተገንጣይ ቡድኑ፥ መንግሥት የያዛቸውን የኖ ፒቲን ቤተሰቦች፣ በስምምነቱ መሠረት በቀጣዮቹ ቀናት ይለቃል፤ ብለው ይጠብቃል።

ተገንጣዮቹ ኃይሎች፥ ከኅዳጣኑ የእንግሊዝኛ ተናጋሪ ካሜሮናውያኑ ወገን ሲኾኑ፣ በፈረንሳይኛ ተናጋሪው አብላጫው የካሜሩን ማኅበረሰብ፣ “መገለል ይደርስብናል” በሚል፣ ከስድስት ዓመታት በፊት መሣሪያ አንሥተው ትግል ጀምረዋል።

በግጭቱ እስከ አሁን፣ ስድስት ሺሕ የሚኾኑ ሰዎች ሲሞቱ፣ 760 ሺሕ ደግሞ ተፈናቅለዋል።

XS
SM
MD
LG