በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ለንደን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የተቃውሞ ሰልፍ


ለንደን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የተቃውሞ ሰልፍ
please wait

No media source currently available

0:00 0:02:17 0:00

በኢትዮጵያ፣ በአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ በተለየ ኹኔታ ይደርሳል፤ ያሉትን በደል ለመቃወም፣ በለንደን አደባባይ ሰልፍ የወጡ ኢትዮጵያውያን፣ የእንግሊዝ መንግሥት በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና እንዲያደርግ ጠየቁ።

ቁጥራቸው እስከ 30 የሚገመት ኢትዮጵያውያን፣ ሰኞ፣ መጋቢት 18 ቀን 2015 ዓ.ም.፣ በእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር መኖሪያ ፊት ለፊት በአካሔዱት ሰልፍ፣ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።

በለንደን ከተማ፣ ሰኞ ዕለት የተደረገው ሰልፍ፣ “በአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ እየተካሔደ ያለው የዘር ማጥፋት ዘመቻ ይቁም” የሚል እንቅስቃሴ ከሚያራምዱ ዘጠኝ ድርጅቶች መሀከል፣ በአራቱ ጥምረት መዘጋጀቱ ተገልጿል።

“የአማራ ግብረ ኃይል” የተሰኘው የዲያስጶራ እንቅስቃሴ፣ በዩናይትድ ኪንግደም ከሚገኙ ሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋራ በመተባበር በአዘጋጁት ሰልፍ፣ ካለፉት አምስት ዓመታት ጀምሮ፣ በኢትዮጵያ በአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ እየተፈጸመ ያሉትን ጥቃት አውግዘዋል።

ባለፈው ሰኞ፣ መጋቢት 18 ቀን 2015 ዓ.ም.፣ በተለምዶ ቁጥር 10 ዳውኒንግ ስትሪት ተብሎ በሚጠራው በእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር መኖሪያ ፊት ለፊት፣ ቁጥራቸው ወደ 30 የሚደርሱ ተሳታፊዎች፣ በተለይ በኦሮሚያ ክልል የአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ አነጣጥሯል፤ ያሉት ግድያ፣ መፈናቀል እና ረኀብ በአስቸኳይ ይቁም፤ በማለት ጠይቀዋል፡፡

ከሰልፍ አስተባባሪዎች አንዱ አቶ እንድርያስ ተስፋዬ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ የአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ እየደረሰ ነው፤ ያሉትን ችግር እንዲቆም ለመጠየቅ የተካሄደ ሰልፍ መኾኑን ተናግረዋል።

ሰልፈኞቹ በመፈክሮቻቸው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናትን በመጥቀስ ተጠያቂ አድርገዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጠን፣ ለንደን የሚገኘውን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጠይቀናል። ኾኖም፣ ስማቸው በይፋ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ሓላፊ፣ ሰላማዊ ሰልፉን በተመለከተ ኤምባሲው፣ ምንም ዐይነት መረጃ ስለሌለው፣ ምላሽ ለመስጠት እንደሚቸገር ገልጸውልናል።

ለእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ደብዳቤ እንደሚያስገቡ፣ ለአሜሪካ ድምፅ በላኩት መግለጫ ያመለከቱት የሰልፉ አስተባባሪ ድርጅቶች፣ ዐዲሱ የሪሺ ሱናክ መንግሥት፣ እየደረሰ ነው፤ ላሉት ችግር ዕውቅና ሰጥቶ በአፋጣኝ ተፈጻሚ የሚኾኑ አስገዳጅ ማዕቀቦችን እንዲጥል በደብዳቤአቸው ጠይቀዋል።

በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት በኩል ደግሞ፣ “በመንግስት ይደገፋል” ያሉት ግድያ እንዲቆም እንዲደረግ፤ ገለልተኛ አጣሪ ኮሚቴ እና ሰላም አስከባሪ ኃይል ጥቃት ወደተፈጸመባቸው አካባቢዎች እንዲሠማራ እና አፋጣኝ ሰብአዊ ድጋፍ ለተጎዱ ኢትዮጵያውያን እንዲደርስ በተጨማሪም፣ መቀመጫቸውን በእንግሊዝ ያደረጉ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት፣ እየተፈጸመ ነው ኢሰብአዊ ያሉትን እንግልት እና ግድያ በስፋት እንዲዘግቡ ጠይቀዋል።

XS
SM
MD
LG