በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

50 ዓመታት ያስቆጠረው የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ አደጋ ላይ ነው


የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ
የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ

ከኢትዮጵያ ጠቅላላ የቆዳ ስፋት 8.5 በመቶ የሚሸፍኑት ብሄራዊ ፓርኮች ውስጥ የሚገኙት የተፈጥሮ ሀብትና የዱር እንስሳት እየተመናመኑ መሆናቸውን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ባለስልጣን አስታውቋል። በተለይ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልሎች መካከል በሚገኘው የባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ ህገ-ወጥ ሰፈራ በመስፋፋቱ መጠለያው በሁለት ዓመት ግዜ ውስጥ ሊጠፋ እንደሚችል የመጠለያው ሀላፊዎች ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።

ሀምሳ አመት ያስቆጠረው የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ ህልውና አደጋ ላይ ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:08:17 0:00

በኢትዮጵያ ካሉ የዱር እንስሳት መጠበቂያ ፓርኮች በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሰው፣ ከተመሰረተ ከ 50 አመታት በላይ ያስቆጠረውና በምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ የሆኑትን ጥቁር ዝሆኖችን ጨምሮ 31 ጡት አጥቢ እንስሳትና ከ222 በላይ የአዕዋፍ ዝርያዎች የሚገኙበት የባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ ዛሬ የመጥፋት አደጋ ተጋርጦበታል።

በኦሮምያና በሶማሌ ክልሎች መሃል የሚገኘውና በኦሮምያ የምስራቅ ሀረርጌ ዞን፣ በሶማሌ ደግሞ የፋይዳና የረር ዞኖች የሚያዋስኑት የባቢሌ መጠለያ በተለይ ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ በክልሎቹ በተፈጠረው የፓለቲካ አለመረጋጋት ምክንያት ግለሰቦች እይተደራጁ በመጠለያው ውስጥ በህገወጥ መንገድ በመስፈራቸው ህልውናው አደጋ ላይ መውደቁን የመጠለያው ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ አደም መሀመድ ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።

በመጠለያው እጅግ እየተባባሰ የመጣውን ህገወጥ ሰፈራ ለማስቆም የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ባለስልጣን ከክልሎቹ ባለስልጣናትና የሀገር ሽማግሌዎች ጋር በመሆን ምስራቅ ሀረርጌ፣ ጅጅጋና ድሬዳዋ ላይ ብዙ ምክክሮች ቢያደርጉም መሬት ላይ የወረደ ለውጥ ግን አልታየም። ይልቁንም የታጠቁ አካላትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች የበለጠ እየሰፈሩ፣ በተለይ ዝሆኖቹን እየገደሉ መሆኑን አቶ አደም ያስረዳሉ።

የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ ሲመሰረት ከ 600 መቶ በላይ ዝሆኖች የነበሩት ሲሆን አሁን 320 ብቻ ቀርተዋል። ከ 6ሺህ 980 ስኩዌር ኪሎሜትር በላይ ይሸፍን የነበርው መጠለያም በህገወጥ ሰፈራው ምክንያት አብዛኛውን ክፍሉን እያጣ ይገኛል። የዱር እንስሳቶቹም መሄጃ ስለሚያጡ የአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ጉዳት ያደርሳሉ።

ከህገወጥ ሰፈራ በተጨማሪ ህገወጥ አደን በባቢሌ መጠለያና በሌሎች ብሄራዊ ፓርኮች የሚገኙ ዝሆኖች ላይ የመጥፋት አደጋ ደቅኗል። ባለፉት ሀያ አመታትም ኢትዮጵያ 90 በመቶ የሚሆኑ ዝሆኖቿን አጥታ፣ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ 1900 ዝሆኖች ብቻ እንደሚገኙ በኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ባለስልጣን የኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ጌትነት ይግዛው ይገልፃሉ።

ኢትዮጵያ ውስጥ የዝሆን ጥርስ ሽያጭ የተከለከለ በመሆኑ የህገወጥ አዳኞቹ ዋና ተቀባዮቻቸው ቻይናና ታይላንድ የመሳሰሉ የሩቅ ምስራቅ አገራት ናቸው። የዝሆን ጥርሶቹም ከተቻለ በአየር መንገድ፣ አለበለዛ በሶማሌላንድ ውይም በጅቡቲ በኩል በህገወጥ መንገድ እንዲወጡ ይደረጋል።

ኢትዮጵያው ውስጥ 13 በፌደራል ደረጃ የሚተዳደሩና 14 በክልሎች የሚተዳደሩ፣ በአጠቃላይ 27 ብሄራዊ ፓርኮች ሲኖሩ ከሀገሪቱ ጠቅላላ የቆዳ ስፋት 8.5 ከመቶ የሚሆነውን ይሸፍናሉ። ነገር ግን ይህን ያክል ስፋት ያላቸውን ብሄራዊ ፓርኮች የሚያስተዳድር በቂ የሰው ሀይልና የገንዘብ አቅም ባለመኖሩ ከዝሆኖች ውጪ ሌሎች የዱር እንስሳትም እየጠፉ መሆናቸውን አቶ ጌትነት አስረድተውናል።

የተፈጥሮ ሀብት መመናመን በዋናነት የሚጎዳው የሰው ልጅን ህልውና መሆኑን የሚገልፁት አቶ ጌትነት፣ ህገ ወጥ ዝውውርን የሚገታ ጠንካራ ህግ ከማውጣት አንስቶ ፓርኮቹ የራሳቸውን ገቢ ማመንጨት የሚችሉባቸው አዋጆች ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርበው ውስኔ እየጠበቁ እንደሆንም ነግረውናል።

ይህን ለሰው ልጆች ህልውና መሰረት የሆነውንና ከፍተኛ የተፈጥሮ ሀብት የያዘውን የባቢሌ ዝሆኖች መጠለያ ለማዳን የኦሮሚያና የሶማሌ ክልሎችን ባለስልጣናት ቀና ርብርብ እንደሚጠይቅ የሚናገሩት የባቢሌ መጠለያ ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ አደም በአጭር ግዜ ውስጥ እርምጃ ካልተወሰደና በህገወጥ መንገድ የሰፈሩት ነዋሪዎች ካልተነሱ፣ መጠለያው በቅርቡ ታሪክ ሊሆን እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

XS
SM
MD
LG