የትግራይ ክልል ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶሱን ጥሪ እንደማይቀበሉ አስታወቁ

Your browser doesn’t support HTML5

በትግራይ ክልል የሚገኙ የአራት አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተላከላቸውን፣ “ተቋርጦ የነበረውን ግንኙነት የማስቀጠል ጥሪ” እንደማይቀበሉት ዛሬ በሰጡት መግለጫ አስታወቁ።

በክልሉ የሰሜን ምዕራብ ትግራይ - ሽረ እንዳሥላሴ፣ የምሥራቃዊ ትግራይ - ዓዲግራት፣ የማዕከላዊ ዞን አኵስም እና የመቐለ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት በመግለጫቸው እንዳስታወቁት፣ በቅዱስ ሲኖዶሱ የተላከው የጥሪ ደብዳቤ፣ በክልሉ ከአንድ ዓመት በፊት ተመሥርቷል፤ ያሉትን “መንበረ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ጠቅላይ ቤተ ክህነት ያገለለ ነው፤” ብለዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ይህን ምላሽ የያዘ ደብዳቤ እስከ አሁን ለመንበረ ፓትርያርኩ እንዳልደረሰ ገልጸው ሲደርስ፤ በቅዱስ ሲኖዶሱ ወይም በቅዱስ ፓትርያርኩ ምላሽ እንደሚሰጥበት ተናግረዋል።