ደቡብ ሱዳን፡- ተመድ “አስፈላጊ እርምጃ” እንዲወስድ ባን ጠየቁ

  • ቪኦኤ ዜና

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባን ኪ ሙን ባለፈው ሣምንት ውስጥ ወደ ጁባ ተጉዘው ሃያ ሺህ ተፈናቃዮች የተጠለሉበትን የመንግሥታቱ ድርጅት ግቢ ጎብኝተዋል፡፡


Your browser doesn’t support HTML5

ደቡብ ሱዳን፡- ተመድ “አስፈላጊ እርምጃ” እንዲወስድ ባን ጠየቁ



ደቡብ ሱዳን ውስጥ ከእንግዲህ የሰላሙን ሂደት የማፋጠን ሥራ የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር እና የአማፂው መሪ ሪያክ ማሻር ጉዳይ ነው ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባን ኪ ሙን አሳሰቡ፡፡

ሚስተር ባን ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ትናንት ያደረጉት ንግግር ለወራት የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆምና አዲስ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ከተስማሙ በጥቂት ቀናት ውስጥ ቢሆንም የስምምነቱ መጣስ ወሬና የሃገሪቱ ዜጎች የሚገኙበት ሁኔታ በእጅጉ እያሳሰባቸው መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ዋና ፀሐፊው ባለፈው ሣምንት ውስጥ ወደ ጁባ ተጉዘው ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪርን አነጋግረል፤ ሃያ ሺህ ተፈናቃዮች የተጠለሉበትን የመንግሥታቱ ድርጅት ግቢንም ጎብኝተዋል፡፡

ተፈናቃዮቹ በመጠለያው ውስጥ እየገፉ ያሉት ሕይወት በእጅጉ ያሳዘናቸው መሆኑን የገለፁት ባን ኪ-ሙን ባለፉት አምስት ወራት ውስጥ በሺሆች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናዊያን መገደላቸውን፣ የጭካኔ አድራጎቶች መፈፀማቸውንና ከአንድ ሚሊየን በላይ ሰው መፈናቀሉንና መሰደዱን ከአምስት ሚሊየን በላይ የሚሆን ሰው የለት ጉርስ የሌለውና አፋጣኝ እርዳታ የሚፈልግ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ለዓርቡ የሰላም ስምምነት መጣስ ሁለቱም ወገኖች እየተወነጃጀሉ ነው፡፡

በሌላ በኩል የደቡብ ሱዳን ቀጣዩ የሽግግር መንግሥት ምን ሊመስል እንደሚችል የሚያሣይ ዕቅድ አንድ የቀድሞ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ሃሣብ አፍላቂዎችና አብላዮች፣ ተንታኞችና የሲቪል ማኅበረሰብ አባላት የሚገኙበት ቡድን አውጥቷል፡፡

ዝርዝሩን ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡