በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላክ የሹመት ደብዳቤያቸውን አቀረቡ

በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሣደር ፓትሪሽያ ሃስላች ለኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ የሹመት ደብዳቤአቸውን ባቀረቡበት ወቅት

በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላክ ዛሬ መስከረም 15 ቀን 2006 ዓ.ም. በብሔራዊ ቤተመንግሥት በተካሄደ ሥነ-ስርዓት የሹመት ደብዳቤያቸውን ለፕሬዚደንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ አቀረቡ፡፡



በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላክ ዛሬ መስከረም 15 ቀን 2006 ዓ.ም. በብሔራዊ ቤተመንግሥት በተካሄደ ሥነ-ስርዓት የሹመት ደብዳቤያቸውን ለፕሬዚደንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ አቀረቡ፡፡

አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ አምባሳደር ሃስላክን ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያስተዋውቅ ቪዲዮ ያዘጋጀ ሲሆን፤ ይህንኑ ቪዲዮ በዩቲዩብ : http://youtu.be/eow93lYhJO8 ላይ ማግኘት ይቻላል፡፡
በከፍተኛ ጥራት የተዘጋጀው የዚህ ቪዲዮ ቅጂ በኤምባሲው ፕሬስ ቢሮ የሚገኝ በመሆኑ፤ ማንኛውም ፍላጎት ያለው አካል ቪዲዮውን ወስዶ ማሰራጨት ይችላል፡፡
የአምባሳደር ሃስላክን የሕይወት ታሪክ ከዚህ ቀጥሎ በቀረበው ጽሁፍ እና በኤምባሲው ድረገጽ፤ http://ethiopia.usembassy.gov/ እንዲሁም የፌስቡክ ገጽwww.facebook.com/us.emb.addisababa ላይ ማግኘት ይቻላል፡፡


ፓትሪሽያ ሃስላች - በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሣደር

የሕይወት ታሪክ
ፓትሪሺያ ኤም. ሃስላክ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር
አምባሳደር ፓትሪሺያ ኤም.ሃስላክ እ.ኤ.አ. ኦገስት 14 ቀን 2013 በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር በመሆን ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ አምባሳደር ሃስላክ ከዚህ ቀደም የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አዲስ ባቋቋመው የግጭት እና መረጋጋት ኦፕሬሽኖች ቢሮ ምክትል ዋና ረዳት ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል፡፡ ከዚያ በፊት ደግሞ አምባሳደር ሃስላክ በውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የስራ አመራር ምክትል ሚኒስትር ጽ/ቤት የኢራቅ ሽግግር አስተባባሪ ነበሩ፡፡ በዚህ ኃላፊነታቸውም በውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ በኩል አሜሪካ በኢራቅ ያደረገችውን ከወታደራዊ ወደ ሲቪል ኦፕሬሽኖች የመሸጋገር ሂደት ከዋሺንግተን አስተባብረዋል፡፡ ይኸው ሂደትም እ.ኤ.አ. በዲሴምበር 2011 መጨረሻ የአሜሪካ ወታደሮች ከኢራቅ ሲወጡ ተጠናቋል፡፡
አምባሳደር ሃስላክ በሽግግር ላይ ባሉ አገራት የሚካሄዱ የልማት ስራዎችን በማስተባበር ረገድ ያካበቱትን ረዥም የስራ ልምድ ይዘው ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡ ከጁን 2010 እስከ ማርች 2011 የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የረሃብ ማስወገድ እና ምግብ ዋስትና መርሃግብር (ፊድ ዘ ፊውቸር) የዲፕሎማሲ ስራ ምክትል አስተባባሪ ሆነው አገልግለዋል፡፡ ከጁላይ 2009 እስከ ጁን 2010 ደግሞ በኢራቅ የአሜሪካ ኤምባሲ የሽግግር ወቅት እርዳታ ጉዳዮች ረዳት አምባሳደር በመሆን የልማት እና የእርዳታ መርሃግብሮችን የማሸጋገር ስራ በበላይነት አስፈጽመዋል፡፡ የአፍጋኒስታን ጉዳይ ቢሮ ዳይሬክተር በነበሩበት እ.ኤ.አ. ከ2002 እስከ 2004፤ አምባሳደር ሃስላክ ብዙ ቢሊዮን ዶላር የወጣበትን የመልሶ ግንባታ መርሃግብር መርተዋል፡፡ ከ2007 እስከ 2009 በኢሲያ ፓሲፊክ የኢኮኖሚ ትብብር መድረክ (አፔክ) የአሜሪካ አምባሳደር ነበሩ፡፡ ከ2004 እሰከ 2007 በላኦስ ሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የአሜሪካ አምባሳደር ነበሩ፡፡ በተጨማሪም በፓኪስታን የኢኮኖሚ ቆንሲል፤ በኢንዶኔዢያ እና ናይጄሪያ ደግሞ ምክትል የኢኮኖሚ ቆንሲል ሆነው አገልግለዋል፡፡ አምባሳደር ሃስላክ የስራ ሕይወታቸውን የጀመሩት በፌዴራሉ መንግስት ውስጥ በግብርና ሚኒስቴር ሲሆን፤ ከ1987 እስከ 1990 የአካባቢው አገራት የግብርና አታሼ በመሆን በሕንድ ተመድበው ነበር፡፡ ከዚህ ምደባ በኋላ ወደ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በመሸጋገር በአውሮፓ ሕብረት የአሜሪካ ልዑክ አባል በመሆን 24 አገራት በአባልነት ለተካተቱበት ቡድን የሚደረግ ድጋፍ መሪ ነበሩ፡፡
አምባሳደር ሃስላክ ባከናወኗቸው ስኬታማ ተግባራት የተነሳ በርካታ ሽልማቶችን ለመሸለም በቅተዋል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2004 በአፍጋኒስታን ላከናወኑት የመልሶ ግንባታ ስራ የተበረከተላቸው የላቀ የክብር ሽልማት፣ እ.ኤ.አ. በ2002 በበጎ ተጽዕኖ እና በአዘጋገብ ወጥነት ያገኙት የዳይሬክተር ጄኔራል ሽልማት፣ በተመሳሳይ ዓመት በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ አፈጻጸም ላበረከቱት እጅግ የላቀ አስተዋጽኦ ያገኙት የኸርበርት ሳልዝማን ሽልማት፤ እንዲሁም በ1998 በጠንካራ የቋንቋ አጠቃቀም እና ተያይዞ ባለው ባሕል ላይ ላደረጉት ጥናት የተሸለሙት የሲንክሌር ላንጉዌጅ ሽልማት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
በኦሬገን፣ የሌክ ኦስዌጎ ተወላጅ የሆኑት አምባሳደር ሃስላክ ስፖኬን፣ ዋሺንግተን ከሚገኘው ጎንዛጋ ዩኒቨርሲቲ፤ በባችለር ኦፍ አርት ዲግሪ የተመረቁ ሲሆን፤ ከኒውዮርኩ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በዓለም አቀፍ ጉዳዮች የማስተርስ ዲግሪ፤ እንዲሁም ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ የምዕራብ አውሮፓ ኢንስቲትዩት ሰርተፊኬት አግኝተዋል፡፡ አምባሳደር ሃስላክ ሺሪን እና ኪራን ኸርበርት የሚባሉ ሁለት ሴት ልጆች እናት ናቸው፡፡ /ምንጭ፡- የአሜሪካ ኤምባሲ፤ አዲስ አበባ - መስከረም 15/2006 ዓ.ም./