በኢትዮጵያ የተደረገው ውይይት አዎንታዊ ርምጃ ታይቶበታል - አይኤምኤፍ

Your browser doesn’t support HTML5

የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ እና የብሔራዊ ባንክ ገዢ ማሞ ምሕረቱ የሚገኙባቸው የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት፣ ከዓለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ አመራሮች ጋራ፣ በአሜሪካ ውይይት እያደረጉ መኾናቸውን አምባሳደር ስለሺ በቀለ ገለጹ፡፡

በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ስለሺ በቀለ/ዶር./፣ እስከ አሁን ድረስ ሰባት ውይይቶች መደረጋቸውን በትዊተር ገጻቸው ጠቅሰዋል፡፡ ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም(አይኤምኤፍ) በበኩሉ፣ ባለሞያዎቹ፣ ባለፈው ሳምንት ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋራ በዐዲስ አበባ ያደረጉት ውይይት፣ አዎንታዊ ርምጃ የታየበት እንደነበር አስታውቋል፡፡

በጉዳዩ ላይ ለአሜሪካ ድምፅ አስተያየት የሰጡት የፋይናንስ ባለሞያው አቶ ኢየሱስወርቅ ዛፉ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማቱ ጋራ የሚያካሒደው ውይይት፣ የልማት ሥራውን ለማከናወን የሚያስችል ብድር ለማግኘት እና የዕዳ ሽግሽግ ለማድረግ እንደሚያግዘው አስረድተዋል፡፡

የኢንቨስትመንት አማካሪው አቶ ያሬድ ኃይለ መስቀል ደግሞ፣ የገንዘብ ተቋማቱ ድጋፍ፣ ከቅድመ ኹኔታ ጋራ ተያይዞ የሚመጣ በመኾኑ ጥንቃቄ እንደሚያስፈልገው ያሳስባሉ፡፡