የቴክኖሎጂ ተደራሽነት ለሴቶች ዕኩልነት ያለው ፋይዳ

Your browser doesn’t support HTML5

በዓለም ዙሪያ ሴቶች በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸው ተሳትፎ ዝቅተኛ መሆኑ የኢኮኖሚ እና የማኅበራዊ ኑሮ ዕኩልነት ላይ ተፅእኖ እያሳደረ መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አስታውቋል። በመሆኑም የመንግሥታቱ ድርጅት ይህ ችግር ትኩረት እንዲያገኝ ብሎም እንዲስተካከል በሚል በዛሬው ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን ያሉትን መሰናዶዎች “ቴክኖሎጂ ለሥርዓተ ጾታ ዕኩልነት” በሚል መሪ ርዕስ እንዲያጠነጥኑ አድርጓል፡፡

በኢትዮጵያም ይህንን ችግር ለመቅረፍ እና በተለይ ወጣት ሴት ተማሪዎች በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ብቁ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ በማስቻል ለማገዝ የተነሳ “ብራይት ጄኔሬሽን” ብሩህ ትውልድ የተሰኘ አዲስ መርኃ ግብር የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎችን በማሰልጠን ላይ ይገኛል። የመርኃ ግብሩ መስራቾች በዩናይትድ ስቴትስ በዋሽንገተን አካባቢ የሚኖሩት ሳይንቲስቶች ዶክተር ብርሃኑ ቡልቻ እና ባለቤቱ ዶክተር ፀጋ ሰለሞን ናቸው፡፡

ዶክተር ብርሃኑ ቡልቻ በዩናይትድ ስቴትስ ብሄራዊ የኤሮኖቲክስ እና የጠፈር ምርምር ድርጅት (ናሳ) በክንዋኔአቸው ስመጥር ተመራማሪ ናቸው፡፡ ባለቤታቸው ዶክተር ጸጋ ሰሎሞንም በታዋቂው የዩናይትድ ስቴትስ የጤና ተቋም (ኤን አይ ኤች) ተመራማሪ ናቸው፡፡ ዶክተር ጸጋ ሰሎሞንን እና በመርኃ ግብሩ አማካይነት ወደኢትዮጵያ ተጉዘው የኮምፒዩተር ፕሮግራሚንግ ስልጠና ከሰጡ የማሳቹሴትስ ቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት(ኤምአይቲ) ተማሪዎች መካከል አንዷ የሆነችው ኔበስ አዳነ ስለ ብሩህ ትውልድ ተልዕኮ ያብራራሉ፡፡