በጣርማ በር ወረዳ በቀጠለው ግጭት ሲቪሎች ለሞት እና ጉዳት እየተዳረጉ መኾኑ ተገለጸ

Your browser doesn’t support HTML5

በመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በአካባቢያቸው የቀጠለው ግጭት፣ ንጹሐን ዜጎችን ለሞት እየዳረገ መኾኑን፣ በሰሜን ሸዋ ዞን የጣርማ በር ወረዳ ነዋሪዎች ተናግረዋል።

ባለፈው ሰኔ 19 ቀን 2016 ዓ.ም. ብቻ እንኳን፣ 14 አርሶ አደሮች መገደላቸውን ያወሱት ነዋሪዎቹ፣ በተለይ ለዚኽኛው ግድያ፣ የመንግሥት የጸጥታ ኀይሎችን ተጠያቂ ፤ አድርገዋል።

የጣርማ በር ወረዳ አስተዳደር፣ ስለ ግድያው መረጃ እንደሌለው ጠቅሶ፣ በአካባቢው ተደጋጋሚ የጸጥታ ችግር መኖሩን ግን አምኗል።

በክልሉ በቀጠለው የትጥቅ ግጭት፣ "ኾን ተብለው የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች አሉ፤" የሚሉት የዐማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ፓርቲ እና በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአማካሪ ቦርድ አባሉ አበባው ደሳለው፣ ኹኔታው እንደሚያሳስባቸው ተናግረዋል፡፡

በ36ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ፣ ተመሳሳይ ጥያቄ ቀርቦላቸው የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ "የጅምላ ግድያ አልተፈጸመም፤ የተወሰኑ ጥፋቶች ተፈጽመው ከኾነ ግን፣ ፈጻሚውን ተጠያቂ እናደርጋለን፤" ማለታቸው ይታወሳል፡፡