ተፈናቃዮች ለወራት ርዳታ እንዳላገኙ ቢገልጹም መንግሥት “ቅሬታው ተጋኗል” አለ

Your browser doesn’t support HTML5

ከኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ተፈናቅለው በደቡብ ወሎ ዞን ተሁለደሬ እና ከላላ ወረዳዎች በመጠለያ ካምፖች ውስጥ እና ከግለሰቦች ጋራ ተጠግተው የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ ምንም ዓይነት ርዳታ ሳያገኙ ዐሥር ወራት እንዳለፋቸው ተናገሩ፡፡

ተፈናቃዮቹ ሕይወታቸውን ለማቆየት ልመናን አማራጭ ማድረጋቸውን ገልጸው፣ በምግብ እጥረት ምክንያት በርካቶች ለጤና ችግር መዳረጋቸውን አመልክተዋል፡፡

የተፈናቃዮቹ ቅሬታ የተጋነነ እንደኾነ የጠቀሰው የደቡብ ወሎ ዞን አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና መምሪያ በበኩሉ፣ “ርዳታው ከወር በላይ አልተቋረጠም፤ አሁንም እየተከፋፈለ ነው፤” ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል፣ በከላላ ወረዳ የሚገኙ ተፈናቃዮች ሕክምና ለማግኘት የጤና መድኅን ክፍያ እንዲከፍሉ መገደዳቸውን ገልጸዋል፡፡ “አሁን ባለንበት ኹኔታ፣ እንኳን ከፍለን ለመታከም ለዕለት ጉርሳችን እንኳን አናገኝም፤” ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡

የሕክምና አገልግሎቱ በነጻ እንደሚሰጥ የጠቆሙት የከላላ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ ሐሰን ይማም ደግሞ፣ ክፍያ የሚጠየቅ ተፈናቃይ ቅሬታውን በአካል ለጽ/ቤቱ ኃላፊ ማቅረብ እንደሚችል አስታውቀዋል፡፡

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ይከታተሉ።